የፕላስቲክ ይዘት የሌላቸውና የተፈጥሮን ሚዛን የሚጠብቁ የቆዳ ምትክ ምርቶችን ከተፈጥሮአዊ የከብት ቆዳ ጋር በሚመሳሰል መልኩ በከፍተኛ ጥራት ማምረት እስካሁን ድረስ ፈታኝ እንደነበር ይታወቃል። ነገር ግን በፊንላንድ የሚገኙ ተመራማሪዎች ይህንን መሰናክል በመሻገር፣ የእንጉዳይ ሥርን (ማይሲሊየም) በመጠቀም በኢንዱስትሪ ማሽኖች አማካይነት በከፍተኛ መጠን የቆዳ መሰል ጨርቃጨርቆችን ማምረት የሚያስችል አዲስ መንገድ ማግኘታቸውን አስታውቀዋል። ይህም ከእንስሳት ነፃ የሆኑና ፕላስቲክ የሌለባቸውን የቆዳ ምትኮች ወደ ሰፊው የዓለም ገበያ ለማቅረብ የተደረገ ትልቅ የሳይንስ ዕርምጃ ነው። በቪቲቲ ፊንላንድ የኢንዱስትሪ ባዮቴክኖሎጂስትና የምግብ ሳይንቲስት የሆኑት ጌዛ ሲልቫይ በኤሲኤስ አፕላይድ ባዮ ማቴሪያልስ ጆርናል ላይ ባስነበቡት የምርምር ውጤት፣ “የእኛ የማምረት ሂደት የታደሱ ጥሬ ዕቃዎችንና መጠነኛ የኬሚካል ሁኔታዎችን ብቻ የሚጠቀም ሲሆን፣ ከእንስሳት እርባታም ሆነ ከፍተኛ ኬሚካል ከሚጠይቁ ሂደቶች ሙሉ በሙሉ ነፃ ነው” ብለዋል። ይህ አሰራር ከባህላዊ የእንስሳት ቆዳ ወይም ከሰው ሰራሽ (ሲንቴቲክ) ቆዳ ማምረቻ ዘዴዎች በጥብቅ የተለየ እንደሆነም አብራርተዋል። ሰው ልጅ ለዘመናት የልብስ፣ የቁሳቁስና የመሳሪያ መስሪያዎችን ለማዘጋጀት የእንስሳትን ቆዳ ሲጠቀም ቆይቷል። በሂደትም የሳይንስ እድገት ከእንስሳት ነፃ የሆኑ ሰው ሰራሽ ቆዳዎችን ማስተዋወቅ ቢችልም፣ እነዚህ ምርቶች ግን ከካርቦን-ነዳጅ (fossil fuel) በሚወጡ ፕላስቲኮች የሚሰሩ በመሆናቸው ለካርቦን ልቀትና ለአካባቢ ብክለት መንስኤ በመሆን ለአስርተ ዓመታት በአፈር ውስጥ ሳይበሰብሱ ይኖራሉ። ይህንን ችግር ለመቅረፍ ተመራማሪዎችና ጥቂት አዳዲስ አምራች ኩባንያዎች የእንጉዳይ ሥር ወይም የማይሲሊየም መዋቅርን ትኩረት ሰጥተው መመርመር ጀምረዋል። ማይሲሊየም ከእንስሳት በደል ነፃ ከመሆኑ ባሻገር፣ በሁለት ሳምንታት አጭር ጊዜ ውስጥ አነስተኛ ውሃና ኤነርጂን ብቻ በመጠቀም በፍጥነት የሚበቅልና በጥቅም ላይ ውሎ ከተጣለ በኋላም ሙሉ በሙሉ በተፈጥሮ መንገድ የሚበሰብስ በመሆኑ ትልቅ የአካባቢ ጥበቃ አጋር ነው። ይህም ተመራማሪዎች ቁሳቁሱን ለዘላቂ ህንፃ ግንባታና ለኤሌክትሮኒክስ እቃዎች ለመጠቀም እንዲመረምሩ ያነሳሳል ። ማይሲሊየም ተሰብስቦ ከተሰራ በኋላ መልኩም ሆነ ባህሪው ከቆዳ ጋር በእጅጉ የሚመሳሰል፣ ለስላሳና የመለጠጥ አቅም ያለው በመሆኑ አምራቾች የፈለጉትን አይነት የላይኛው ገጽ ቅርጽና ቀለም ሊሰጡት ይችላሉ። ባህላዊው አሰራር ማይሲሊየምን በቀጥታ በማሳደግ በኩል የወፍራምነት አለመመጣጠንና የመቀደድ ችግር ነበረበት። ይህንን ለመፍታት ሲልቫይና ቡድናቸው ማይሲሊየሙን ፈሳሽ ውስጥ አሳድገው እርጥብ ፓልፕ ካዘጋጁ በኋላ፣ ለስላሳነቱን ከሚጨምረው ሶርቢቶልና ጥንካሬ ከሚሰጠው ሴሉሎስ ጋር በመደባለቅ ወደ ቀጭን ወረቀቶች ዘረጉት። በዚህም በሮል-ቱ-ሮል የኢንዱስትሪ ሂደት በደቂቃ እስከ አንድ ሜትር የሚደርስ ቁሳቁስ ማምረት የተቻለ ሲሆን፣ ጥንካሬውም ከተፈጥሮ ቆዳ ጋር የተቃረበ ሆኗል። ምንም እንኳን አሁንም የመቀደድና የመቧጨር መቋቋም አቅሙን ለማሻሻል ተጨማሪ ምርምር የሚፈልግ ቢሆንም፣ አሰራሩ ከአካባቢ በካይ ሰው ሰራሽ ቆዳዎች ነፃ ለሆነ ዘላቂ የቆዳ ምትክ ትልቅ ተስፋ ጥሏል።
___
ሀሳብ እና‘ሳ‘ፍራለን
ምላሽ ይስጡ