ነሐሴ 25 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ) በኔፓል ኑዋኮት አውራጃ በሚገኘው ትሪቡቫን ትሪሹሊ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ47 ዓመቱ ርዕሰ መምህር ራጄንድራ ዳዋዲ ያሳዩት ፈጣን ውሳኔ ሰጪነት እና ቆራጥነት የበርካታ ህፃናትን ህይወት ሊቀጥፍ ይችል የነበረውን ታላቅ አደጋ አስቀርቷል። ርዕሰ መምህር ራጄንድራ ከሂማላያ ተራሮች የመነጨ ከባድ የጎርፍ ማዕበል ወደ ትምህርት ቤቱ አቅጣጫ እየገሰገሰ መሆኑን የሚገልጽ አስቸኳይ የስልክ ማስጠንቀቂያ እንደደረሳቸው፣ ምንም አይነት ጊዜ ሳያባክኑ የትምህርት ቤቱ ደወል በኃይል እንዲመታ አዘዋል። በወቅቱ በትምህርት ቤቱ ቅፅረ ግቢ ውስጥ ይማሩ የነበሩ ከ900 በላይ ተማሪዎች እና መምህራን ወዲያውኑ ትምህርታቸውን አቋርጠው ወደ ተራራማና ደህንነቱ የተጠበቀ ቦታ እንዲሸሹ ተደርጓል። በተጨማሪም ርዕሰ መምህሩ በትምህርት ቤት ባስ በመጓዝ ላይ የነበሩ ከ700 በላይ ተማሪዎችን የጫኑ ተሽከርካሪዎችን በስልክ በማነጋገር ወዲያውኑ ወደኋላ እንዲመለሱ በማድረግ፣ በአጠቃላይ ከ1,600 በላይ ተማሪዎችን ከከፋ አደጋ ማዳን ችለዋል። ተማሪዎቹ ግቢውን ለቀው በወጡ በአስር ደቂቃዎች ውስጥ የጭቃ እና የውሃ ማዕበሉ ባለ 3 ፎቅ የትምህርት ቤቱን ህንፃ ሙሉ በሙሉ ጠራርጎ ወስዶታል። በአደጋው ወቅት በትምህርት ቤቱ ውስጥ ከነበሩት ተማሪዎች መካከል ምንም አይነት የአካል ጉዳት ወይም የህይወት ማጣት ሳይከሰት በደህንነት ወደ ቤተሰቦቻቸው መመለሳቸው የተረጋገጠ ሲሆን፣ የርዕሰ መምህሩ የጀግንነት ስራ በሀገሪቱ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ አድናቆትን አትርፎላቸዋል።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ