ትራምፕ ለእስራኤል ማስጠንቀቂያ መስጠታቸው ተሰማ
ሰኔ 02 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ) የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ጠንከር ያለ ማስጠንቀቂያ መለገሳቸውን ይፋ አድርገዋል። እስራኤል ከኢራን ጋር የምታደርገውን ጦርነት በድጋሚ የምትቀሰቅስ ከሆነ አሜሪካ እንደማትደግፋትና ብቻዋን ልትቀር እንደምትችል ትራምፕ ያስጠነቀቁ ሲሆን ለአክሲዮስ የዜና ወኪል በሰጡት መግለጫም “ቢቢ፤ ጥንቃቄ ብታደርግ ይሻላል፤ ካልሆነ ግን በቅርቡ ብቻህን ልትቀር ትችላለህ” ሲሉ በስልክ ጥሪያቸው ወቅት በግልጽ መናገራቸውን አረጋግጠዋል።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ ይህንን ማስጠንቀቂያ የሰጡት ቀጥተኛ ትዕዛዝ ለማስተላለፍ ሳይሆን የኔታንያሁን ውሳኔ ለመገደብ መሆኑን ገልጸው እኔ ያልኩት ነገር ቢኖር አዕምሯችንን መጠቀም አለብን የሚል ብቻ ነው ካሉ በኋላ በአሁኑ ወቅት ከኢራን ጋር በጣም ጠንካራ እና ጥሩ ስምምነት ለመፈረም መቃረባቸውን ጠቁመዋል። በተጨማሪም እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከመፈጸሟ ጥቂት ቀደም ብሎ ለአሜሪካ መንግስት አጭር መረጃ መስጠቷን ትራምፕ ገልጸው ይሁን እንጂ የጦር አውሮፕላኖቹ ቀድሞውኑ ወደ ስምሪት አቅንተው በነበረበት በዚያ አጣዳፊ ሰዓት ጭምር ጣልቃ በመግባት ጥቃቱ ውስን እና የተገደበ እንዲሆን ማድረጋቸውን ይፋ አድርገዋል።
ይህ በትራምፕ እና በኔታንያሁ መካከል የተፈጠረው አለመግባባት ይፋ የሆነው አሜሪካ ከኢራን ጋር ዲፕሎማሲያዊ ስምምነት ላይ ለመድረስ ከፍተኛ ግፊት እያደረገች ባለችበት ወቅት ሲሆን በአንጻሩ ኔታንያሁ ኢራን በድጋሚ ጥቃት የምትሰነዝር ከሆነ ጠንካራ ወታደራዊ ርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ መሆናቸውን በገለጹበት ወቅት በመሆኑ በሁለቱ መሪዎች መካከል ያለው ስትራቴጂካዊ ልዩነት ከቀን ወደ ቀን እየሰፋ መምጣቱን ተንታኞች እየገለጹ ይገኛሉ።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ