ሐምሌ 24 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ) የስልታዊ ቡድን ምክክር እስከ ትላንት ቀጥሎ እንደዋለም የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን አስታውቋል።
በሀገራዊ ምክክር ጉባኤው 250 አባላት ባሉት 16 ስልታዊ ቡድኖች የተደራጁ ተመካካሪዎች ምክክር እስከ ትላንት ሐምሌ 23/2018 ዓ.ም ቀጥሎ መዋሉንም ኮሚሽኑ ገልጿል፡፡
በ250 አባላት የተደራጁ 16 ስልታዊ ቡድኖች ከጥቃቅንና ንዑስ ቡድኖች በተገኙና በተጠናቀሩ የአጀንዳ ምክረ ሀሳቦች ላይ ከሐምሌ 22/2018 ዓ.ም ጀምረው ነው ምክክር ያደረጉት፡፡
ሐምሌ 22/2018 ዓ.ም በነበረው የምክክር ውሎ ከእያንዳንዱ ስልታዊ ቡድን በተመረጡ 25 የአጀንዳ ምክረ ሀሳብ አጠናካሪዎች አማካኝነት የተጠናቀሩ ምክረ ሀሳቦችን ያዳመጠው 16ቱ ባለ 250 አባላት ስልታዊ ቡድን፣ በጥቃቅንና በንዑስ ቡድኖች ተነስተው በቀረበው ቃለ ጉባኤ ላይ ያልተካተቱ፣ በአግባቡ ያልተብራሩ ያላቸውን ሀሳቦች ማቅረቡ አይዘነጋም፡፡
ስልታዊ ቡድኖቹ በውሏቸው የተሰጡ አስተያየቶች ተካተውበት በድጋሚ የተደራጀውን ቃለ ጉባኤ የጋራ በማድረግ በቀጣይ ለሚደረገው እና 500 ተመካካሪዎችን ለያዙ 8 ቡድኖች ምክክር ዝግጅት ሲያደርጉ ውለዋል፡፡
በዛሬው ዕለት ደግሞ በሀገራዊ ምክክር ጉባኤው የውሳኔ አሰጣጥ ሂደት ላይ እገዛ የሚያደርጉ የክልል፣ የከተማ መስተዳድር እና የፌዴራል ተወካዮች ምርጫ እንደሚደረግም ኮሚሽኑ ባጋራው መረጃ አስታውቋል፡፡
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ