ሚያዚያ 12 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ)የአማራ ክልል መንግሥት ያቀረበውን የሰላም ጥሪ ተቀብለው ወደ መደበኛ ሕይወታቸው የሚመለሱ ታጣቂዎች ቁጥር እየጨመረ ቢሆንም፣ አሁንም በአንዳንድ አካባቢዎች የሚፈጸሙ እገታዎችና ዘረፋዎች በነዋሪዎች ላይ ስጋት መፍጠራቸውን የክልሉ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ኃላፊ ዶክተር እሸቱ ዮሴፍ ለመናኸሪያ ሬዲዮ እንደገለጹት፣ እስካሁን ከ31 ሺህ በላይ ታጣቂዎች የሰላም አማራጩን ተቀብለው ከማኅበረሰቡ ጋር ተቀላቅለዋል።
ይሁን እንጂ በአንዳንድ የከተማና የገጠር አካባቢዎች ታጣቂዎች አሁንም ዜጎችን የማገት፣ የማፈንና የመዝረፍ ተግባራትን እየፈጸሙ ይገኛሉ። ምንም እንኳ እነዚህ ሕገ-ወጥ ድርጊቶች ሙሉ በሙሉ ባይቆሙም፣ ካለፉት ወራት አንጻር ሲታይ ግን ከፍተኛ መሻሻል መኖሩን ኃላፊው ገልጸዋል።
የትምህርት ሥርዓቱን የሚያስተጓጉሉ፣ ዜጎችን የሚያግቱና አገርን የሚያፈርሱ ተግባራትን በመቃወም፣ በርካታ ታጣቂዎች “ከእንግዲህ አገሬን አላፈርስም” በሚል ቁርጠኝነት የሰላም አማራጩን እየመረጡ መሆኑንም ዶክተር እሸቱ አክለው ተናግረዋል።
በክልሉ የሚንቀሳቀሰው የታጣቂ ቡድን ከኤርትራ መንግሥትና ከሌሎች የታጠቁ ኃይሎች ጋር ትብብር እንደሚኖረው የጠቆሙት ኃላፊው፣ በአሁኑ ወቅት በቢሮው ሥልጠና ወስደው ማኅበረሰቡን ከተቀላቀሉት በተጨማሪ፣ ትጥቃቸውን ፈትተው ሥልጠና ለመውሰድ በመጠባበቅ ላይ ያሉ ዜጎች መኖራቸውንም አስታውቀዋል።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ