መጋቢት 24 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ)በህክምናው ዓለም ሳይንሳዊ ልብ ወለድ የሚመስል ግን ደግሞ እውን የሆነ አዲስ ግኝት ይፋ ሆኗል። በሰሜን ምዕራብ ፣ ራይስ (Rice) እና ካርኔጊ ሜሎን (Carnegie Mellon) ዩኒቨርሲቲዎች የተውጣጡ ተመራማሪዎች በሰውነት ውስጥ ተቀብሮ መድኃኒት የሚያመርት “ሆቢት” (HOBIT) የተሰኘ ጥቃቅን መሣሪያ ሰርተዋል።
እ.ኤ.አ ማርች 27 ቀን 2026 በዲቫይስ (Device) የተሰኘ የሳይንስ መጽሔት ላይ የወጣው ይህ ጥናት እንደሚያሳየው፣ መሣሪያው በውስጡ የያዛቸውን ህያው ሴሎች በመጠቀም ሶስት የተለያዩ መድኃኒቶችን በአንድ ጊዜ ማምረት ይችላል። እነዚህም የኤችአይቪ (HIV) መከላከያ አንቲቦዲ፣ የስኳር በሽታን ለመቆጣጠር የሚረዳ ጂኤልፒ-1 (GLP-1) ፔፕታይድ እና የምግብ ፍላጎትን የሚቀንሰው ሌፕቲን (leptin) ናቸው።
ይህ መሣሪያ እንደ ማስቲካ ቀጭንና ትንሽ ሲሆን፣ በውስጡ ያሉትን ሴሎች ከሰውነታችን የበሽታ መከላከያ ሥርዓት ጥቃት ይከላከላል። ከዚህም በላይ በአካባቢው ያሉ የውሃ ሞለኪውሎችን በመሰንጠቅ ለሴሎቹ የሚያስፈልጋቸውን ኦክስጅን ራሱ ማመንጨት መቻሉ ልዩ ያደርገዋል። በጥናቱ ወቅት በመሣሪያው ውስጥ የነበሩት 65 በመቶ የሚሆኑት ሴሎች ለአንድ ሙሉ ወር በህይወት መቆየት ችለዋል።
የጥናቱ መሪ ጆናታን ሪቭኔይ እንደገለጹት፣ ይህ ቴክኖሎጂ ታካሚዎች መድኃኒት የመርሳት ስጋት እንዳይኖራቸው ከማድረጉም ባለፈ፣ በሰውነት ውስጥ የማያቋርጥና የተመጣጠነ የመድኃኒት መጠን እንዲኖር ያስችላል። ይህም ወደፊት “የመድኃኒት ቤት” አገልግሎት በሰውነታችን ውስጥ ብቻ እንዲወሰን በር የሚከፍት ትልቅ እመርታ ተደርጎ ተወስዷል።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ