የኢሬቻ በዓል ከገዳ ሥርዓት ጋር እንደሚገናኝና በኦሮሞ ማኅበረሰብ ዘንድ ለዘመናት ሲከበር እንደቆየ የታሪክ ምሁራን ይናገራሉ። በዓሉ መስከረም ከገባና የመስቀል በዓል ከተከበረ በሳምንቱ ቅዳሜ እለት በአዲስ አበባ ከተማ ሆራ ፊኒፊኔ ሲከበር፣ እሁድ እለት ደግሞ በቢሾፍቱ ከተማ ሆራ ሃርሰዲ ይከበራል።
የኢሬቻ በዓል በርካታ ባህላዊና ማኅበራዊ እሴቶችን የያዘ ሲሆን፣ ሴቶች በዓሉ ላይ ሳር በመያዝ ከፊት የሚቀድሙበት ባህል አንዱ የእሴቱ መገለጫ መሆኑ ይነገራል። ማኅበረሰቡ ወደ ወንዙ ሲሄድ “መሬዎ! መሬዎ!” (ፈጣሪን በማመስገን) በማለት እርጥብ ሳር ይዘው በማቅናት፣ “ከጨለማው ወደ ብርሃን ያሸጋገርን ፈጣሪ” በማመስገን እንዲሁም እርቅ፣ ሰላም፣ አንድነትና ምስጋና በማድረግ በዓሉን ያከብራሉ።
በዓሉ ላይ ሰላምን የሚያወርዱና እርቅ እንዲመጣ የሚለምኑ ሀዳ ሲንቄዎች ከአባ ገዳዎች ፊት በመሄድ ወደ መልካ የሚደረገውን ጉዞ የሚመሩ መሆኑ፣ በገዳ ሥርዓት የሴቶችን እኩልነትና ክብር በተግባር የሚገልጽበት መሆኑን ያሳያል።
በዚህ በዓል ላይ ሀዳ ሲንቄዎች ትልቅ ድርሻ እንዳላቸው የሚናገሩት ሀዳ ሲንቄ ሮዛ ገመቹ፣ በዓሉ ለሴቶች ትልቅ ቦታ እንዳለውም ያነሳሉ። ሀዳ ሲንቄ ሮዛ በዓሉን ለማኅበራዊ ትስስርና ለሰላም ግንባታ መጠቀም እንደሚያስፈልግ ገልጸው፣ “ሰላም የሁሉ ነገር መሠረት በመሆኑ ለሕዝብ እንታገላለን የሚሉ ሁሉ የሰላም መንገድን እንዲመርጡ” አሳስበዋል። በኢትዮጵያ ያሉ ባህላዊ የዳኝነት ሥርዓቶች ቀላል የማይባሉ ቅራኔዎችን በመፍታት ከፍተኛ ሚና እንዳላቸው በማንሳት፣ “ኢሬቻ ሰላም መሆኑን ተረድቶ እንደ ሀገር ሰላም እንዲኖር መሥራት ያስፈልጋል” ብለዋል።
በበጋ ወቅትና በክረምት የሚከበር የኢሬቻ በዓል በኦሮሞ ማኅበረሰብ ዘንድ ለዘመናት ሲከበር መቆየቱን የተናገሩት የኦሮሞ ቱለማ አባ ገዳ ጎበና ኦልኣሬሶ ናቸው። ማንኛውም የኦሮሞ ማኅበረሰብ በዓሉን ለማክበር ከመምጣቱ በፊት በአካባቢው የተጋጩ ሰዎች ካሉ እርቅ እንዲያወርዱ እንደሚደረግ ገልጸው፣ ከዚያ በኋላ ለማመስገን ከቤታቸው እንደሚወጡ አስረድተዋል። ኢሬቻ የአንድነት፣ የመከባበር፣ የፍቅርና የሰላም በዓል መሆኑ የሁሉም ማኅበረሰብ በዓል እንደሚያደርገው ተናግረዋል። ወጣቱ በዓሉ በሰላም እንዲከበር የራሱን አስተዋጽኦ ሊያደርግ እንደሚገባ በማሳሰብ፣ በበዓሉ ላይ በገዳ ሥርዓት የተከለከሉ ነገሮችን ማድረግ እንደማይገባም አስገንዝበዋል። በበዓሉ ላይ አዛውንት፣ ሕፃናት፣ ልጃገረዶችና ወጣቶች ሁሉም ከቤታቸው ወጥተው “ከጭጋጋማው ጊዜ ወደ ጸደይ ያደረሰንን እናመሰግናለን” በሚል በዓሉን እንደሚያከብሩ ገልጸዋል። በዓሉ ባህሉን ጠብቆ ለቀጣይ ትውልድ እንዲተላለፍ ሁሉም መሥራት እንደሚጠበቅበትም ተናግረዋል።
የኢሬቻ በዓል ከኦሮሞ ማኅበረሰብ በተጨማሪ ሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች እየተረዱትና ወንድማማችነትን ለማጠናከር እየተሳተፉ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የባህል ጥናት ተመራማሪ ዶክተር ጥላሁን ተሊላ ናቸው። በዓሉ ዓለም አቀፍ ገጽታ ያላቸው እሴቶች እንዳሉት ያነሱት ዶክተር ጥላሁን፣ በዚህም ምክንያት በየዓመቱ በርካታ ዜጎች በበዓሉ ላይ እየተገኙ እንደሚያከብሩ ገልጸዋል። በዓሉ ለጥቁር አፍሪካውያን የሚጠቅም ጭምር መሆኑን በመግለጽ፣ ያለንን ሀብት ለሀገር መጠቀም ይቻላል የሚለው በስፋት እየተሰራበት መሆኑን አንስተዋል። እንደ ሀገር ያሉ ባህሎችን ማስተዋወቅ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ እንዳለው በመግለጽ፣ ኢሬቻ እሴቱን ጠብቆ እንዲቀጥል ዩኒቨርሲቲዎች በጋራ ሆነው ስለ በዓሉ በማጥናት ማኅበረሰቡ ግንዛቤ እንዲኖረው እየሠሩ መሆናቸውን አስረድተዋል።
ኢሬቻ አንዱ የገዳ ሥርዓት መገለጫ መሆኑን ያነሱት ደግሞ በአርሲ ዩኒቨርሲቲ የኦሮሞ ጥናት ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር ዶክተር ሙሐመድ ነሞ ናቸው። በኢሬቻ በዓል ሴቶች ትልቅ ድርሻ እንዳላቸው የገለጹት ዶክተር ሙሐመድ፣ በበዓሉ ላይ ለሴቶች ቅድሚያ የሚሰጥበት ባህል መኖሩን አክለዋል። በዓሉ ብዝኃነትን የሚያስተናግድ ሥርዓት በመሆኑ ብሔር ብሔረሰቦች ሊሳተፉና አብረው ሊያከብሩ እንደሚገባ ገልጸዋል። በኢሬቻ በዓል ላይ የተጠኑ ጥናቶች በቂ አለመሆናቸውን በመግለጽ የበዓሉን ትርጉም ብቻ ሳይሆን በዓሉ ለሀገር ግንባታ ያለውን ሚና ሊጠና እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ያልተነኩ የሀገር በቀል እውቀቶችን ጥናት በማድረግ ማሳደግና ሀገሪቱን ማስተዋወቅ እንደሚያስፈልግም አንስተዋል። የኢሬቻን ትርጉም የሆነውን ሰላምና ወንድማማችነትን ለአለም ሀገራት ማስተዋወቅና ባህሉን ማሳደግ እንደሚገባም ተናግረዋል። ኢሬቻ በተለያዩ ጊዜያት ከ150 ዓመት በላይ ተቋርጦ እንደነበር ያስታወሱት ዶክተር ሙሐመድ፣ በዓሉ መከበር ከጀመረ በኋላ እሴቱን ጠብቆ እንዲሄድ እየተሰራበት መሆኑን አክለዋል።
የኦሮሚያ ቱሪዝም ኮሚሽን የእቅድ ክትትል፣ በጀትና ግምገማ ዳይሬክተር አቶ ነጋሽ ሰሎሞን በበኩላቸው፣ የኢሬቻ በዓል ለትውልድ እንዲተላለፍ ሀዳ ሲንቄዎችና አባ ገዳዎች በተለያዩ መድረኮች ላይ መረጃዎችን እየሰጡ እና ምሁራንም ጥናታዊ ጽሑፎችን በማድረግ ዜጎች ስለ በዓሉ ግንዛቤ እንዲኖራቸው እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ኢሬቻን ማኅበረሰቡ ሳይከፋፈል እያከበረው መሆኑን በመግለጽ፣ በዓሉን ለማክበር የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች እንደሚመጡም አስረድተዋል። የሀገሪቱን መልካም ገጽታ ለመገንባት ከሚጠቅሙ ሥራዎች መካከል አንዱ በዓላት መሆናቸውን የገለጹ ሲሆን፣ ኮሚሽኑ በዓሉ ሲቃረብ ኢሬቻን የተመለከቱ የተለያዩ ዝግጅቶችን እያካሄደ መሆኑን አስታውቀዋል።
በኦሮሞ ማኅበረሰብ ዘንድ የሚከበረው የኢሬቻ በዓል የእርቅ፣ የሰላም፣ የወንድማማችነት እና ያለፈውን ዓመት በማመስገን የወደፊቱን የሚሰንቅበት በዓል መሆኑን አባ ገዳዎች አውስተዋል። ይህን በዓል ከኦሮሞ ማኅበረሰብ ውጪ ያሉ ሌሎች የማኅበረሰብ ክፍሎች የሚሳተፉበትና ወንድማማችነት የሚጠነክርበት መሆኑን የኦሮሚያ ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ኃይሉ አዱኛ ተናግረዋል። የወንድማማችነትና የኅብረ ብሔራዊነት የሚገለጽበት፣ አንዱ የሌላውን ባህል በማክበር አብሮ የሚሳተፍበት ጭምር መሆኑን ያነሱት ኃላፊው፣ በዓሉን ብሔር ብሔረሰቦች ተገናኝተው ማክበራቸው ሕዝባዊ ትስስርን እንደሚጨምር ገልጸዋል። ኢሬቻ ማኅበራዊ ትስስርን ከመፍጠርም ባሻገር የቱሪዝም ዘርፉ እንዲነቃቃና የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች በዚህ አጋጣሚ የቱሪስት መስህቦችን እንዲጎበኙ ዕድል እንደሚፈጥር ተናግረዋል። ኢሬቻ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ጠቀሜታም እንዳለው ያነሱት ኃላፊው፣ በዓሉን በተለያዩ መልኩ የማስተዋወቅ ሥራ እየተሰራ መሆኑንም አክለዋል።
በመጨረሻም፣ የሰላም፣ የእርቅና የወንድማማችነት በዓል የሆነው ኢሬቻ በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲታወቅና እንደ ሀገር ያሉ የሰላም ችግሮች እንዲፈታበት አባ ገዳዎች፣ ሀዳ ሲንቄዎችና ሌሎችም አካላት ሊሠሩበት እንደሚገባ በዳሰሳው ሐሳባቸውን የሰጡት አካላት ተናግረዋል።
በመዲና አውሰኢድ
ምላሽ ይስጡ