ሰኔ 04 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ)ኢትዮጵያ የዓለም የክህሎት ማኅበር አባል መሆኗን ተከትሎ፣ በሀገር ውስጥ የሚካሄዱ የክህሎት ውድድሮች ደረጃቸውን ጠብቀው እስከ ዓለም አቀፍ መድረክ የሚዘልቁበት ግልጽ አሠራር መዘርጋቱን ያስታወቁት የኢፌዴሪ የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ብሩክ ከድር ናቸው። ዋና ዳይሬክተሩ ለጣቢያችን እንደገለጹት፣ የሀገር ውስጥ ልምምድ ወሳኝ በመሆኑ በየሁለት ዓመቱ የሚካሄደው የክህሎት ውድድር መቀጠሉን በመጥቀስ፤ ኢትዮጵያ እስካሁን ጥናቶችንና የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ያካተቱ አራት ዙር የክህሎት ውድድሮችን ማካሄድ መቻሏን ገልጸዋል።
በአሁኑ ወቅት ሀገሪቱ የዓለም የክህሎት ማኅበር አባል መሆኗን በማንሳት፤ ውድድሩ በሀገር ደረጃ ብቻ የሚያበቃ ሳይሆን፣ ከክልል እስከ ፌዴራል አልፎም ግልጽ በሆነ መንገድ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚካሄድበት ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን አስረድተዋል።
በቴክኖሎጂ ሽግግር ላይ ያሉ ቁልፍ ችግሮችን በመለየት የኢንዱስትሪውን ዘርፍ ማሳደግ እንደሚገባ የጠቆሙት ዋና ዳይሬክተሩ፤ አሁን ላይ ከ16 ሀገራት የተውጣጡ አካላት የሚሳተፉበት ውድድር መሆኑን በማንሳት፣ ይህም የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትን በመሳብ ረገድ የራሱ አስተዋጽኦ እንዳለው አብራርተዋል።

ሰልጣኞች ሥልጠናቸውን ሲያጠናቅቁ የገንዘብ እጥረት እንዳይገጥማቸው የፋይናንስ አቅርቦት የመስጠት ሥራ ትኩረት ተሰጥቶታል ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ተቋሙ ባጠናው ጥናት መሠረት በመደበኛና በአጫጭር ሥልጠናዎች ወደ ዘርፉ የሚመጡ ሰልጣኞች ቁጥር 6 ሚሊዮን መድረሱንም አመላክተዋል።
ውድድሩ በዚህ መልክ ሲካሄድ ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑን የኢፌዴሪ የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ገልጿል።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ