ግንቦት 26 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ) በቁሶች ሳይንስ እና በኤሌክትሮኒክስ ምህንድስና ዘርፍ ታላቅ አብዮት ይፈጥራል የተባለለት በ”ግራፊን” ላይ የተመሰረተ የኃይል ማከማቻ ቴክኖሎጂ የዓለማችንን ትኩረት እየሳበ ይገኛል። ይህ ቁስ ባለው እጅግ ከፍተኛ የኤሌክትሪክ አስተላላፊነት እና የሙቀት መቋቋም አቅም ምክንያት፣ ኃይልን አሁን ካሉት መደበኛ የባትሪ ስርዓቶች በበለጠ ፍጥነትና በከፍተኛ ብቃት ማዘዋወር ያስችላል።
የግራፊን ዋነኛው ድንቅ ባህሪ የሚመነጨው ከአቶሚክ መዋቅሩ ሲሆን በአንድ የካርቦን አቶም ውፍረት ብቻ የተሰራጨው ይህ ቁስ ለዓዮን ልውውጥ የሚሆን እጅግ ሰፊ የገጽታ ስፋት ያቀርባል። ይህ ልዩ ተፈጥሮው እንደ ስልኮች ያሉ ተንቀሳቃሽ ኤሌክትሮኒክሶችን እና የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን በደቂቃዎች ውስጥ በፍጥነት ለመሙላት የሚያስችል በመሆኑ በአሁኑ ወቅት የባትሪ ዘርፍ ያለበትን ትልቅ የፍጥነት እጥረት ሙሉ በሙሉ ይቀርፋል።
ከፈጣን የኃይል መሙላት አቅሙ ባሻገር ግራፊን ከፍተኛ ሙቀትንና አካላዊ ጫናዎችን የመቋቋም ልዩ ብቃት አለው። በአሁኑ ጊዜ የምንጠቀምባቸው የሊቲየም-አዮን ባትሪዎች ከመጠን በላይ ሲሞቁ የመፈንዳትና እሳት የመነሳት ስጋት ያለባቸው ቢሆንም ግራፊን ግን ሙቀትን በእኩል በማሰራጨት ባትሪዎች ደህንነታቸው የተጠበቀ እና በከፍተኛ ሙቀት ውስጥም እንኳ አስተማማኝ እንዲሆኑ ያደርጋል ነው የተባለው።
የቁሱ ጠንካራነት የባትሪዎችን ዕድሜ በከፍተኛ ደረጃ የሚያራዝመው ሲሆን ባትሪዎች ጥቅማቸውን ሳይቀንሱ እና ሳይበላሹ በብዙ ሺህ ለሚቆጠሩ ጊዜያት ደጋግመው እንዲሞሉና እንዲሰሩ ያስችላቸዋል። ይህም በተደጋጋሚ ባትሪ የመቀየርን ወጪ ከመቀነሱም በላይ ለአካባቢ ጥበቃና ለዘላቂ ኤሌክትሮኒክስ አጠቃቀም ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረክታል።
በአሁኑ ወቅት የሳይንስ ሊቃውንት እና የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ዋነኛ ትኩረት የግራፊን ባትሪዎችን ጥራት ሳይቀንሱ በከፍተኛ መጠን በፋብሪካ ማምረት ላይ ነው። ይህ የማምረት ሂደት እውን ሆኖ ወጪው በሚቀንስበት ጊዜ የግራፊን ባትሪዎች የዓለማችን አዲስ፣ ፈጣን እና ደህንነቱ የተጠበቀ የኃይል ማከማቻ መለኪያ መሆናቸው የማይቀር ነው ተብሏል።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ