መጋቢት 14 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ)አርሰናል በክረምቱ የዝውውር መስኮት ቤን ዋይትን በሽያጭ ዝርዝር ውስጥ ሊያካትተው እንደሚችል የሚጠቁሙ ጭምጭምታዎች መደመጥ መጀመራቸውን ተከትሎ፣ የሮማውን ተከላካይ ዌስሊ ፍራንካን እንደ ተተኪ መመልከት መጀመሩን የሚጠቁሙ መረጃዎች ወጥተዋል።
ምንም እንኳን ቤን ዋይት በአሁኑ ወቅት በአሰልጣኝ ሚኬል አርቴታ ስር ወሳኝ ሚና የሚጫወት ተጫዋች ቢሆንም፣ ዘንድሮ የመሰለፍ ዕድሉ እየተመናመነና ቦታውን ለዩሪየን ቲምበር ያስረከበ ይመስላል። ክለቡ ለወደፊቱ የረጅም ጊዜ ዕቅድ በማውጣት የ22 ዓመቱን ብራዚላዊ ተከላካይ በቅርበት እየተከታተለ ይገኛል።
ዌስሊ ፍራንካ በዘንድሮው የ2025/26 የውድድር ዘመን በሮማ ቤት በሁሉም ውድድሮች 31 ጨዋታዎችን ያደረገ ሲሆን፣ በሴሪ አው በ24 ጨዋታዎች ላይ ተሰልፏል። ተከላካዩ በዘንድሮው የውድድር ዘመን 88.2% የተሳካ ኳስ የማቀበል ስኬት እና በአማካይ በጨዋታ 2.3 ኳሶችን የማቋረጥ ስኬት አስመዝግቧል። በተጨማሪም በመስመር ላይ በሚያደርጋቸው የማጥቃት እንቅስቃሴዎች በአጠቃላይ 4 ኳሶችን ለቡድን አጋሮቹ አመቻችቶ አቀብሏል። ፍራንካ ካለው ፍጥነትና ጉልበት አንጻር፣ በአርሰናል የቀኝ መስመር ተከላካይ ቦታ ላይ ከቤን ዋይት ጋር ተመሳሳይ የሆነ ግን ደግሞ ይበልጥ በዕድሜ ወጣት የሆነ አማራጭ ሊሆን እንደሚችል ታምኖበታል።
በሌላ በኩል ቤን ዋይት በአሁኑ ወቅት አርሰናል ፕሪምየር ሊጉን እንዲመራና በ4 የዋንጫ ፉክክር ውስጥ እንዲገኝ ካደረጉ ተጫዋቾች መካከል አንዱ ነው። ዋይት በዘንድሮው የውድድር ዘመን በ28 የሊግ ጨዋታዎች 2 ግቦችን ሲያስቆጥር፣ 5 ኳሶችን ደግሞ አመቻችቶ በማቀበል ወጥ የሆነ ብቃት እያሳየ ይገኛል። አርሰናል ተጫዋቹን የመሸጥ አስገዳጅ ፍላጎት ባይኖረውም፣ በክረምቱ ከፍተኛ የዝውውር ጥያቄ ከቀረበለት ግን ዌስሊ ፍራንካን ለማስፈረም ድርድር ሊጀምር እንደሚችል ይጠበቃል።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ