በመካከለኛው ምስራቅ በእስራኤል እና በኢራን መካከል ከሰሞኑ የተፈጠረው ከፍተኛ ውጥረት የአለምን የድፍድፍ ነዳጅ ገበያ በእጅጉ አንቀጥቅጧል። እነዚህ ግጭቶች ወደ ሰፊ ጦርነት ሊያመሩ ይችላሉ የሚለው ስጋት፣ ከነዳጅ የበለጸገው ክልል የሚመጣው አቅርቦት ሊስተጓጎል ይችላል የሚል ስጋት በመፍጠሩ የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቷል። አሁን ባለው ሁኔታ፣ የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ ከ7% በላይ ጭማሪ አሳይቷል።
በተለይም፦
ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ (Brent crude)፣ የአለም አቀፍ መለኪያ ተደርጎ የሚወሰደው፣ ከ7% በላይ ከፍ ብሏል። በአንድ ወቅት ከ10% በላይ ጭማሪ አሳይቶ ከጥር ወር ወዲህ ከፍተኛው ደረጃ ላይ ደርሶ ነበር።
የአሜሪካ ዌስት ቴክሳስ ኢንተርሚዲየት (WTI) ድፍድፍ ነዳጅ ደግሞ 7.3% ጨምሯል።ይህ ጭማሪ ሁለቱንም ቤንችማርኮች በዚህ ሳምንት ከፍተኛውን የዕለት ውስጥ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ አድርጓል፤ ይህም ከ2022ቱ የሩሲያ-ዩክሬን ጦርነት ወዲህ ያልታየ ክስተት ነው ተብሏል።
ለጭማሪው እንደምክንያት የሚጠቀሱ ጉዳዮች መካከል አንደኛው የአቅርቦት ስጋት ሲሆን ኢራን የአለምን 5% የሚሆነውን የነዳጅ አቅርቦት የምታቀርብ ዋናዋ አምራች ሀገር ነች። በእስራኤል እና በኢራን መካከል የሚፈጠር ማንኛውም ወታደራዊ ግጭት የኢራንን የነዳጅ ምርት እና ኤክስፖርት ሊያስተጓጉል ይችላል የሚል ስጋት እንዳለ ተመላክቷል።
የሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ (Strait of Hormuz): ይህ የባህር ወሽመጥ ከአለም አቀፍ የነዳጅ ምርት ውስጥ ወደ 20% የሚጠጋው በየቀኑ የሚያልፍበት ስትራቴጂካዊ የንግድ መስመር ነው።
ውጥረቱ ከጨመረ ኢራን ይህንን የባህር ወሽመጥ መዝጋት ወይም የነዳጅ መርከቦችን ማወክ ትችላለች የሚል ስጋት አለ፤ ይህም በአለም አቀፍ የነዳጅ አቅርቦት ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ያሳድራል።
የኢንቨስተሮች ፍራቻ👉በአካባቢው ያለው የፖለቲካ አለመረጋጋት የኢንቨስተሮችን እምነት የሚነካ ሲሆን፣ ይህ ደግሞ በገበያ ላይ የነዳጅ ዋጋ እንዲጨምር ያደርጋል።
የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ መጨመር በብዙ ዘርፎች ላይ ሰፊ ተጽዕኖ ሊያሳድር ይችላል። ከነዳጅ ዋጋ መጨመር ጀምሮ እስከ የምግብ ዋጋ ድረስ የኑሮ ውድነት ሊያስከትል ይችላል። እንደ አየር መንገድ እና የመርከብ ኩባንያዎች ያሉ ከፍተኛ ነዳጅ የሚጠቀሙ ንግዶች ከፍተኛ ኪሳራ ሊደርስባቸው ይችላል።
የአለም አቀፉ ማህበረሰብ ውጥረቱ ተባብሶ ወደ ሰፊ ግጭት እንዳያድግ ከፍተኛ ስጋት ውስጥ ገብቷል። ተንታኞች እንደሚሉት፣ ግጭቱ ከቁጥጥር ውጭ ከሆነ የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በአንድ በርሜል ከ$80 እስከ $100 ሊደርስ ይችላል። ሆኖም፣ እንደዚህ አይነት ከፍተኛ ጭማሪ ሲከሰት ሌሎች የነዳጅ አምራቾች ምርታቸውን በመጨመር ዋጋውን የመቆጣጠር አቅም ሊኖራቸው እንደሚችልም ይጠበቃል።
በአጠቃላይ፣ በመካከለኛው ምስራቅ ያለው ወቅታዊ ውጥረት የነዳጅ ገበያውን በማናጋት የአቅርቦት ስጋቶችን እና የዋጋ መጨመርን አስከትሏል ነው የተባለው።
ሁኔታው ከቁጥጥር ውጪ እንዳይሆን እና ተጨማሪ የኢኮኖሚ ውድመትን ለመከላከል የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ክትትሉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል።
በጌታሁን አስናቀ
ምላሽ ይስጡ