ላሚን ያማል ከስፔን ብሔራዊ ቡድን ስብስብ ውጪ መሆኑ ተረጋገጠ
ሕዳር 02 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ) የስፔን ብሔራዊ ቡድን እና የባርሴሎና እግር ኳስ ክለብ በላሚን ያማል ጉዳይ የገቡበት ውዝግብና አለመግባባት እንደቀጠለ ይገኛል።
ወጣቱ ተጫዋች ላሚን ያማል በመስከረም ወር በነበረው የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታዎች ላይ ለሀገሩ ከተሰለፈ በኋላ ወደ ክለቡ ሲመለስ በደረሰበት ጉዳት ምክንያት ለሦስት ሳምንታት ከሜዳ መራቅ መገደዱ ይታወሳል። በዚህም ምክንያት የባርሴሎናው አሰልጣኝ ሃንሲ ዲተር ፍሊክ፣ ተጫዋቹ ጉዳት እያለበት እንዲጫወት በመደረጉ ተቃውሟቸውን በመግለጽ በስፔን እግር ኳስ ፌዴሬሽን እና በብሔራዊ ቡድኑ አሰልጣኝ ሉዊስ ዴ ላ ፉዌንቴ ላይ ከባድ ትችት መሰንዘራቸው አይዘነጋም።
ተጫዋቹ ከጉዳቱ ሙሉ በሙሉ ሳያገግም እየተጫወተ እንደነበር መናገር ይቻላል። ስፔን ለሚኖሯት ሁለት የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታዎች በአሰልጣኝ ዴ ላ ፉዌንቴ ጥሪ ደርሶት ስብስቡን ከተቀላቀለ በኋላ፣ የብሔራዊ ቡድኑ የሕክምና ባለሙያዎች የተጫዋቹን የጤና ሁኔታ ሲያጣሩ አሁንም በጉዳት ላይ እንደሚገኝ አረጋግጠዋል።
የሕክምና ክፍሎቹ ባደረጉት ምርመራ፣ ጉዳቱ ከ7 እስከ 10 ቀናት የሚወስድ እረፍት እንደሚያስፈልገው በመወሰን፣ ላሚን ያማል የብሔራዊ ቡድኑን ካምፕ (ስብስብ) ለቆ ወደ ክለቡ እንዲመለስ ፈቃድ ተሰጥቷል።
ክለቡ ባርሴሎና የተጫዋቹን የሕመም ሁኔታ ሪፖርት ለብሔራዊ ቡድኑ የላከው ተጫዋቹ ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ጥሪ በተደረገለት ዕለት መሆኑ፣ በሁለቱ ተቋማት ማለትም በባርሴሎና እና በስፔን እግር ኳስ ፌዴሬሽን መካከል ያለውን የመረጃ ልውውጥ ክፍተት በግልጽ ያሳያል። ይህ ደግሞ በሁለቱ ተቋማት መካከል አለ የተባለውን ቅራኔና አለመግባባት ይበልጥ ያጎላል።
አሰልጣኝ ዴ ላ ፉዌንቴ ግን በጉዳዩ ላይ ዝምታን መምረጥ አልፈለጉም። ከሀገሪቱ ተነባቢ አምድ ከሚባለው RNE Deportes ጋር ባደረጉት ቆይታ፣ በሁኔታው መደናገጣቸውንና እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ገብተው እንደማያውቁ ገልጸዋል። “ምንም ትንፍሽ ሳይሉ ቆይተው ደብዳቤ ይነግሩሃል” ሲሉ የባርሴሎና እግር ኳስ ክለብ ላይ ጣታቸውን ቀስረዋል።
በአጠቃላይ፣ የላሚን ያማል የአካል ብቃት (Fitness) ሁኔታ ጥያቄ የሚነሳበት ሲሆን፣ ጥቅምት ወር በነበረው የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ላይም ሀገሩን መወከል አለመቻሉ ይታወሳል።
የስፔን ብሔራዊ ቡድን (ላ ፉሪያ ሮሃ) በቀጣይ የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታዋን ከቱርክ እና ከጆርጂያ ጋር የምታከናውን ይሆናል።
የቴሌግራም ቻናላችን ይቀላቀሉ 👉 https://t.me/menaharia_fm
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን 📞
👉011-639-28-52
👉011-639-37-63 (https://stream.zeno.fm/yw8poig9iwtuv)