መጋቢት 25 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ)ጣሊያን ከኢራን ጋር ለታቀደው ጦርነት የጦር መሳሪያ የጫኑ የአሜሪካ የጦር አውሮፕላኖች በሲሲሊ በሚገኘው ሲጎኔላ (Sigonella) የጦር ሰፈር እንዳያርፉ መከልከሏ ተሰማ። ይህ ያልተጠበቀ ውሳኔ የተላለፈው አሜሪካ የፈቃድ አሰጣጥ ደንቦችን አልተከተለችም በሚል ሲሆን፣ ጉዳዩ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ወታደራዊ ግንኙነት ወደ አዲስ ውጥረት ውስጥ ከቶታል።
የጣሊያን ባለስልጣናት እንደገለጹት፣ የአሜሪካ የቦምብ ጣይ አውሮፕላኖች በሲጎኔላ ለማረፍ ጥያቄ ያቀረቡት አውሮፕላኖቹ በበረራ ላይ እያሉ ነው። ይህም የጣሊያን ፓርላማ ፈቃድ ለመስጠት በቂ ጊዜ እንዳይኖረው አድርጓል ተብሏል። በ1950ዎቹ በተፈረመው ስምምነት መሰረት፣ በጣሊያን የሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮች ለሎጂስቲክስ እና ለስልጠና ብቻ የሚያገለግሉ እንጂ ለአደጋ ጊዜ ካልሆነ በስተቀር የጦር መሳሪያ ለማጓጓዣነት ሊውሉ እንደማይችሉ ተጠቅሷል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሜሎኒ በሰጡት መግለጫ፣ ውሳኔው ቀደም ሲል የነበሩ ስምምነቶችን መሰረት ያደረገ መሆኑን ገልጸው፣ ከዩናይትድ ስቴትስ ጋር ያለው ግንኙነት ግን “ጠንካራ እና ሙሉ ትብብር ላይ የተመሰረተ” መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። ይሁን እንጂ ይህ እርምጃ በጣሊያን ብቻ የተገደበ ሳይሆን፣ ስፔን እና ፈረንሳይ ተመሳሳይ የአሜሪካ ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችን እየገደቡ ባሉበት ወቅት የተከሰተ በመሆኑ በአውሮፓ ያለውን አጠቃላይ የፖለቲካ ሁኔታ አሳሳቢ አድርጎታል።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ