መጋቢት 24 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ)በአውሮፓዊቷ ሀገር ስዊዘርላንድ እና በአሜሪካ መካከል ያለው የቢሊዮን ዶላር የጦር መሳሪያ ግዢ ስምምነት አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱ ተሰምቷል። ስዊዘርላንድ ከአሜሪካ ለመግዛት አቅዳው የነበረውን ዘመናዊ የፓትሪዮት ሚሳኤል መከላከያ ስርዓት ትዕዛዝ ሙሉ በሙሉ የመሰረዝ አማራጭ እንዳላት በይፋ ገልጻለች።
ይህ ውሳኔ ሊመጣ የቻለው አሜሪካ ለስዊዘርላንድ ልታቀርብ የነበረውን የሚሳኤል መከላከያ ለሌላ ሀገር ቅድሚያ ለመስጠት ማሰቧን ተከትሎ የመጣ ተቃውሞ እንደሆነ ተጠቁሟል። ስዊዘርላንድ ለሀገሪቱ የአየር ክልል ጥበቃ ወሳኝ ነው ያለችውን ይህን ቴክኖሎጂ በወቅቱ የማታገኝ ከሆነ ስምምነቱን ወደ ጎን በመተው ሌሎች አማራጮችን እንደምትመለከት አስታውቃለች።
የስዊዘርላንድ መንግስት ባለስልጣናት እንደገለጹት ከሆነ አሜሪካ የገባችውን ቃል የማታከብር ከሆነና የአቅርቦት መዘግየት የሚፈጠር ከሆነ ሀገሪቱ በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላር የምታወጣበትን ይህን ፕሮጀክት በድጋሚ ለመመርመር ተገድዳለች። ጉዳዩ በሁለቱ ሀገራት ዲፕሎማሲያዊ እና ወታደራዊ ግንኙነት ላይ መጠነኛ መሻከር መፍጠሩም ተነግሯል።
የፓትሪዮት ሚሳኤል መከላከያ ስርዓት በአለም ላይ ካሉ ዘመናዊ የአየር መከላከያ መሣሪያዎች አንዱ ሲሆን ስዊዘርላንድም ለረጅም ጊዜ ስትጠብቀው የነበረ ፕሮጀክት ነው። ሆኖም አሁን ላይ የተፈጠረው አለመግባባት ስምምነቱ እንዲፈርስ ወይም እንዲራዘም ሊያደርገው እንደሚችል ተገምቷል።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ