በአዲስ አበባ ከተማ የላፍቶ ሰማይ ሥር በሚገኝ አንድ አነስተኛ ቢሮ ውስጥ የሚሰማው የፒያኖ ድምፅ ተራ የሙዚቃ ዜማ አይደለም። ያ ድምፅ በስደት አውድማ ተቀጥቅጠው የተመለሱ፣ በደላሎች ተስፋ ተበልተው ባዶ እጃቸውን የቀሩ እና በማኅበራዊ መገለል ስቃይ ውስጥ የነበሩ ሴቶች አዲስ የሕይወት እስትንፋስ ነው። ይህ ስፍራ “ምሳሌ” ሪተርንስ ኤንድ ፖቴንሻል ማይግራንት አርት ኦርጋናይዜሽን ሲሆን፣ በውስጡም እንደ ሊያ ሻረው ያሉ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ተጋላጭ ወገኖችን የታደሰ ታሪክ ይዟል። የሊያ ታሪክ የብዙ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ነጸብራቅ ነው።
በአዲስ አበባ ወረዳ 20 ተወልዳ ያደገችው ሊያ፣ በልጅነቷ ነጭ ጋውን ለብሳ ሰዎችን የምታክም ሐኪም የመሆን ሕልም ነበራት። ይሁን እንጂ የቤተሰብ የመጀመሪያ ልጅ መሆኗ የጫነባት ኃላፊነት እና እናቷ ዳቦና እንጀራ በመሸጥ የምታገኘው ገቢ ካለው የኑሮ ውድነት ጋር አለመመጣጠኑ ሕልሟን አጨልሞ ወደ ስደት እንድታማትር አደረጋት።
ሊያ ወደ ስደት እንድታመራ ካደረጓት ገፊ ምክንያቶች መካከል የአየር ንብረት ለውጥና ተያያዥ የኢኮኖሚ ጫናዎች ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛሉ። ምንም እንኳን ሊያ የከተማ ነዋሪ ብትሆንም፣ በኢትዮጵያ በተለያዩ አካባቢዎች የሚከሰቱ ድርቆችና የተፈጥሮ መዛባቶች በግብርናውና በንግዱ ዘርፍ ላይ የሚያሳድሩት ተጽዕኖ፣ የኑሮ ውድነትን በማናር እንደ ሊያ ያሉ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን የከተማ ነዋሪዎችንም ጭምር ለተዘዋዋሪ የኢኮኖሚ ቀውስ ይዳርጋል።
በዚህ መሃል ደላሎች “በአንድ ዓመት ውስጥ ባለሀብት ትሆኚያለሽ” የሚል የሐሰት ተስፋ ሰንቀው ቀረቧት። ሊያ በአጎቷ ልጅ ላይ ያየችው የወርቅና የገንዘብ ብልጭልጭ ተስፋዋን ይበልጥ አቀጣጠለው። ይሁን እንጂ እግሯ የአረብ አገርን ምድር እንደረገጠ የገጠማት እውነታ ከሕልሟ ፍጹም ተቃራኒ ነበር። እልም ያለ ገጠር ውስጥ በቀን ለረጅም ሰዓታት እየለፋች በወር የምታገኘው 1,500 የኢትዮጵያ ብር ብቻ ነበር።
እንዲያውም የሥድስት ወር ደመወዟ ተከልክሎ በሕገ-ወጥ መንገድ ወደ ሌላ ስፍራ ለመሸሽ ስትገደድ፣ በደላሎች እጅ የወደቀ ሕይወት ምን ያህል መራራ እንደሆነ ተገነዘበች።
የአየር ንብረት ለውጥና የሰዎች ዝውውር ስላላቸው ቁርኝት ጥናት የሚያደርጉ ባለሙያዎች እንደሚገልጹት፣ የአካባቢ መዛባት የዜጎችን የመቋቋም አቅም በማዳከም ለሕገ-ወጥ አዘዋዋሪዎች ሲሳይ ያደርጋቸዋል። በዘርፉ የረጅም ጊዜ ልምድ ያላቸው አንድ ስማቸውን መናገር ያለፈለጉ የፍልሰት ጉዳዮች ባለሙያ እንደሚሉት፦ “የአየር ንብረት ለውጥ ‘የአደጋ ማባባሻ’ ነው። ግብርናው ሲታወክና መደበኛ የገቢ ምንጮች ሲጠፉ፣ ደላሎች ይህንን ተጋላጭነት በመጠቀም ዜጎችን ወደ ባርነትና ብዝበዛ ይወስዷቸዋል። በተለይም ሴቶችና ሕፃናት ለዚህ አደጋ ይበልጥ ተጋላጭ ናቸው።”ብለዋል።
ይህ የባለሙያ ትንታኔ እንደ ሊያ ያሉ ወጣቶች ለምን በቀላሉ በደላሎች ወጥመድ ውስጥ እንደሚወድቁ ሳይንሳዊ ማብራሪያ ይሰጠናል። በአረብ አገርና በሱዳን ለ15 ዓመታት የቆየችው ሊያ፣ በሱዳን የተቀሰቀሰው ጦርነት ሕይወቷን ዳግም ወደ አዘቅት ከተተው። ባዶ እጇን ወደ አገሯ ስትመለስ የገጠማት ማኅበራዊ ጫና ከስደቱ ስቃይ የከፋ ነበር። ጎረቤቶቿ “መቼ ነው የምትመለሺው?” እያሉ የሚሰነዝሩት ወሬና ስላቅ ለከፍተኛ የሥነ-አእምሮ ጭንቀት ዳረጋት።
ታናናሾቿ አገር ውስጥ ሰርተው ራሳቸውን ሲለውጡ፣ እሷ ግን ከዜሮ መጀመሯና ካለፈው ጸጸት ጋር መታገሏ ከቤት መውጣት እስክትጠላ ድረስ አዳክሟት ነበር። በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ነበር “ምሳሌ” የተባለውና በፍልሰት ተመላሾች የሚመራው ድርጅት የደረሰላት። የድርጅቱ መሥራች ሕይወት ዳግም፣ እራሷም ለዘጠኝ ዓመታት በአረብ አገር ስደት መከራን የቀመሰችና በሙዚቃ ሕክምና ራሷን የፈወሰች ጠንካራ ሴት ነች። ሕይወት በ”ፍሪደም ፈንድ” (Freedom Fund) ድጋፍ ባቋቋመችው በዚህ ማዕከል፣ እንደ ሊያ ያሉ ሴቶች በሙዚቃና በሥነ-ጥበብ አማካኝነት ከደረሰባቸው የስሜት ስብራት እንዲያገግሙ ታደርጋለች።
በኢትዮጵያ በሰው የመነገድ እና ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር ወንጀልን ለመከላከል ሰፊ የሕግ ማዕቀፎች ተዘርግተዋል። ከእነዚህም መካከል አዋጅ ቁጥር 1178/2012 (የሰዎች ዝውውርንና ስደተኞችን በሕገ-ወጥ መንገድ ድንበር የማሻገር ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የወጣ አዋጅ) ቀዳሚው ነው። ይህ አዋጅ በሰው በሚነግዱ አዘዋዋሪዎች ላይ ከ15 እስከ 25 ዓመት የሚደርስ ጽኑ እስራትና እስከ 150 ሺህ ብር የሚደርስ የገንዘብ መቀጫ ይደነግጋል።

ሕይወት ዳግም እንደምትገልጸው፣ ብዙዎች ይህንን ጠንካራ ሕግ ቢያውቁ ኖሮ ከወንጀሉ ይቆጠቡ ነበር። ድርጅቷ ይህንኑ ሕግ መሠረት በማድረግ ለተመላሾችና ለተጋላጭ ወገኖች ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ ይሰራል። በዚህ ረገድ ዜጎች ትክክለኛ መረጃ የሚያገኙባቸው የመንግሥት ተቋማት ሚና ቁልፍ ነው።
ለተመላሾች ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ድጋፍ ለመስጠት እና መልሶ ለማቋቋም የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ዋነኛው ተጠሪ ሲሆን፣ በውጭ አገር የሥራ ስምሪት ዙሪያ ሕጋዊና አስተማማኝ መረጃ ለመስጠት የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ግንባር ቀደም ተቋም ነው።
በሰው የመነገድና ሕገ-ወጥ ዝውውር (TIP and SOM) ወንጀሎች ላይ ተገቢውን ሕጋዊ ምላሽ ለመስጠት ደግሞ የፍትህ ሚኒስቴር በዋናነት ይሰራል::
የዓለም አቀፉ የፍልሰት ድርጅት (IOM) በኢትዮጵያ የሚጫወተው ሚናም ከዚህ ጋር የተቆራኘ ነው። IOM ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በመተባበር መደበኛና ሰብዓዊነት የተሞላበት ፍልሰትን ለማስፈን ይሰራል። በተለይም “CREATE” የተሰኘው ፕሮጀክት የአየር ንብረት ለውጥ ለሰዎች ዝውውር ያለውን አስተዋጽኦ በማጥናትና ተጋላጭ ማኅበረሰቦችን በማጠናከር ረገድ ትልቅ እምርታ እያሳየ ይገኛል።
ድርጅቱ ለጋዜጠኞች የሚሰጠው ሥነ-ምግባራዊ የዘገባ አቀራረብ ሥልጠና፣ ተጎጂዎችን ሳያገልና ሳይሸማቅቅ ታሪካቸውን ለዓለም ለማሳየት ትልቅ አቅም ሆኗል።
አሁንም ቢሆን በሱዳን በኩል የሚደረጉ ሕገ-ወጥ ጉዞዎች ለበርካታ ኢትዮጵያውያን ሴቶች መከራ ሆነው ቀጥለዋል። በጉዞው ወቅት የሚፈጸሙ የአስገድዶ መድፈር ወንጀሎች፣ ለኤች አይ ቪ ኤድስ መጋለጥና የሞት አደጋዎች አሁንም በስፋት ይስተዋላሉ።
ሊያ ሻረው “በሕገ-ወጥነት በፍጹም አያዋጣም፣ አትሞክሩት” ስትል የምትመክረው ከመራራ የሕይወት ተሞክሮ ተነስታ ነው። ዛሬ ሊያ በምሳሌ ድርጅት ባገኘችው ሥልጠና ታግዛ በዲዛይን ሥራ ላይ ተሰማርታለች፤ ትዳር መሥርታ የሁለት ልጆች እናት ሆና ሰላማዊ ሕይወት እየመራች ትገኛለች።
ይህ ስኬት የሚያሳየው፣ ተመላሾች ተገቢው ድጋፍና የሥነ-ልቦና ሕክምና ካገኙ አገር ውስጥ ሰርቶ መለወጥ እንደሚቻል ነው።
ባጠቃላይ፣ የሰዎች ዝውውርን ለመግታት የመንግሥት ተቋማት፣ እንደ IOM ያሉ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች፣ የ”ምሳሌ” ዓይነት ተጎጂ-መራሽ ማኅበራት እና የሚዲያ ተቋማት በቅንጅት መስራት እንደሚኖርባቸው ተመላክቷል።
ማኅበረሰቡ ለተመላሾች ያለውን ዝቅተኛ አመለካከት በመቀየር፣ እንደ አዲስ ራሳቸውን እንዲገነቡ ማበረታታት ይኖርበታል። ማንኛውም ዜጋ በሰው የመነገድ ጥርጣሬ ሲኖረው ወይም መረጃ ሲፈልግ 8797 ነፃ የጥቆማ መስመርን ወይም 6073 የፍትህ ቢሮ የጥሪ ማዕከልን በመጠቀም የድርሻውን ሊወጣ ይገባል ተብሏል። የሊያ ታሪክ እንዳስተማረን፣ ስደት መዳረሻው ባዶ እጅ ቢሆንም፣ በኅብረትና በፈውስ ድልድይነት ግን የጠፋውን ተስፋ ዳግም ማለም ይቻላል።
በጌታሁን አስናቀ
ምላሽ ይስጡ