መጋቢት 09 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ)በመካከለኛው ምስራቅ ሆርሙዝ ባህረ ሰላጤ አካባቢ የተቀሰቀሰው ወታደራዊ ውጥረት በዓለም አቀፍ የነዳጅ አቅርቦት ላይ ከፍተኛ ቀውስ አስከትሏል። እስያ ከምታገኘው የነዳጅ ፍላጎት 90 በመቶ የሚሆነው የሚያልፍበት ይህ መስመር በመስተጓጎሉ ምክንያት ስሪላንካ ከመጋቢት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ረቡዕን ጨምሮ የሥራ ቀናትን ወደ አራት ዝቅ በማድረግ ትምህርት ቤቶችን፣ ፍርድ ቤቶችንና የመንግሥት መስሪያ ቤቶችን ዘግታለች። በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ የነዳጅ ቁጠባ የታወጀ ሲሆን ለአንድ መኪና በሳምንት 15 ሊትር፣ ለሞተር ብስክሌት ደግሞ 5 ሊትር ብቻ እንዲፈቀድ ተወስኗል።
ይህ አስከፊ ቀውስ በስሪላንካ ላይ ብቻ ሳይወሰን ሌሎች የእስያ አገራትም አስገራሚ እርምጃዎችን እንዲወስዱ አስገድዷቸዋል። ታይላንድ ዜጎቿ የኃይል ፍጆታን ለመቀነስ ሲሉ ቀለል ያሉ ልብሶችን እንዲለብሱና የአየር ማቀዝቀዣዎችን እንዲቀንሱ አሳስባለች። ማይናማር በበኩሏ የግል ተሽከርካሪዎች በፈረቃ ብቻ እንዲንቀሳቀሱ የገደበች ሲሆን ፓኪስታን ደግሞ ትምህርት ቤቶች ሙሉ በሙሉ በኢንተርኔት ብቻ ትምህርት እንዲሰጡ አዛለች። በተጨማሪም ባንግላዴሽ የበዓላት ቀናትን በማሻሻል የኃይል ቁጠባ ስልቶችን በመተግበር ላይ ትገኛለች።
ይህ በሺዎች ኪሎ ሜትሮች ርቆ በሚገኝ ቀጠና የተከሰተ አንድ ግጭት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን የዕለት ተዕለት ኑሮ እንዴት በቀላሉ ሊያናጋ እንደሚችል ትልቅ ማሳያ ሆኗል። ዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ መናርም ለሌሎች አህጉራት በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ላሉ በማደግ ላይ ያሉ አገራት የኑሮ ውድነት ስጋት መሆኑ አልቀረም።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ