መጋቢት 08 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ)የአንቶኒ አልባኒዝ የሚመራው የአውስትራሊያ መንግስት በመካከለኛው ምስራቅ ያለውን የነዳጅ መስመር ደህንነት ለመጠበቅ አሜሪካ ላቀረበችው ጥሪ “መርከብ አንልክም” ሲል በይፋ ምላሽ ሰጠ። ይህ የአውስትራሊያ ውሳኔ የተሰማው፣ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ድጋፍ ያልሰጡ አጋር ሀገራትን “ለወደፊት አልረሳቸውም” ሲሉ ጠንከር ያለ ማስጠንቀቂያ በሰጡ ማግስት ነው።
እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በየካቲት 2026 መጨረሻ ላይ በኢራን እና በአሜሪካ-እስራኤል ጥምረት መካከል የተቀሰቀሰውን ጦርነት ተከትሎ፣ ወሳኙ የሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ ለትራንስፖርት ዝግ መሆኑ ይታወቃል። ፕሬዝዳንት ትራምፕ ይህንን የነዳጅ መስመር ለማስከፈትና የነዳጅ ጫኝ መርከቦችን ደህንነት ለመጠበቅ አጋር ሀገራት የባህር ኃይል መርከቦቻቸውን እንዲልኩ ግፊት እያደረጉ ይገኛሉ።
የአውስትራሊያ የትራንስፖርት ሚኒስትር ካትሪን ኪንግ ሰኞ መጋቢት 16 ቀን 2026 (እ.ኤ.አ.) በሰጡት መግለጫ፣ ሀገራቸው ለመካከለኛው ምስራቅ የባህር ኃይል መርከቦችን የመላክ እቅድ እንደሌላት አረጋግጠዋል። ይሁን እንጂ አውስትራሊያ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ለሚገኙ ዜጎቿ ከለላ ለመስጠት የ”E-7A Wedgetail” የስለላ አውሮፕላን እና የሚሳኤል መከላከያ ድጋፎችን እያደረገች መሆኗን ገልጸዋል።
ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው፣ አጋር ሀገራት የራሳቸውን የኢነርጂ ፍላጎት ለማስጠበቅ ካልተባበሩ ጉዳዩ “ለኔቶ (NATO) ህልውና አስጊ ነው” ሲሉ አስታውቀዋል። አውስትራሊያ መርከብ ላለመላክ የወሰነችው በአሁኑ ወቅት ያሏት የጦር መርከቦች ለጥገና በመቆማቸው እና በክልሉ ያለው ግጭት ይበልጥ እንዳይባባስ ስጋት ስላላት እንደሆነ የጦር መኮንኖች ገልጸዋል።
ከአውስትራሊያ በተጨማሪ እንደ ጃፓን፣ ጀርመን እና እንግሊዝ ያሉ ሀገራትም ቀጥተኛ የባህር ኃይል ተሳትፎ ለማድረግ እያመነቱ ሲሆን፣ ይህም በአሜሪካ እና በአጋሮቿ መካከል ያለውን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ውጥረት ውስጥ ከቶታል።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ