ታህሳስ 15 ቀን 2018(መናኸሪያ ሬዲዮ)የሊቢያ ጦር ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ሌተናል ጄነራል መሀመድ አል-ሃዳድ በቱርክ በደረሰ አሰቃቂ የአውሮፕላን አደጋ ህይወታቸው ማለፉ ተሰማ። ጄነራሉ በአንካራ የነበራቸውን ይፋዊ የስራ ጉብኝት አጠናቅቀው ወደ ትሪፖሊ በመመለስ ላይ እያሉ የተሳፈሩባት ፋልኮን 50 የተባለች የግል ጄት አደጋ እንደደረሰባት ተገልጿል።
የሊቢያ ጠቅላይ ሚኒስትር አብዱልሃሚድ ድቤባህ እንደገለጹት አደጋው የተከሰተው በቴክኒክ ብልሽት ምክንያት ሲሆን በአደጋው ወቅት ከአዛዡ በተጨማሪ አራት ከፍተኛ የጦር መኮንኖች እና ሶስት የበረራ ሰራተኞች በድምሩ ስምንት ሰዎች ህይወታቸው አልፏል። ከሟቾቹ መካከል የሊቢያ ምድር ጦር አዛዥ ሜጀር ጄነራል አል-ፊቱሪ ግሬቤል እና የወታደራዊ ማኑፋክቸሪንግ ባለስልጣን ዳይሬክተር ብሪጋዴር ጄነራል ማህሙድ አል-ቃታዊ እንደሚገኙበት ታውቋል።
አውሮፕላኑ ከአንካራ ኤሰንቦጋ አውሮፕላን ማረፊያ ተነስቶ ጥቂት ቆይታ ካደረገ በኋላ የኤሌክትሪክ ብልሽት እንዳጋጠመው ለቁጥጥር ማማው ሪፖርት አድርጎ እንደነበር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የቱርክ ባለስልጣናት በአሁኑ ወቅት በአደጋው ዙሪያ ሰፊ ምርመራ እያደረጉ ሲሆን የሊቢያ መንግስትም ለደረሰው አደጋ የሶስት ቀናት ብሄራዊ የሃዘን አዋጅ አውጇል።
ምላሽ ይስጡ