ሙሉ ፕሮግራሙን በድምጽ ለመስማት ከታች ያለውን ኦዲዮ ይጫኑ
በአለም አቀፍ ደረጃ እድሜን፣ ፆታን፣ የአኗኗር ሁኔታ እና ሌሎችንም ልዩነቶች ሳይመርጥ የዜጎችን ህይወት እየቀጠፈ ያለው ተላላፊ ያልሆነ በሽታ አሁንም አሳሳቢነቱ እንደቀጠለ ነው።
የልብ ህመም፤ ካንሰር፣ ሥር የሰደዱ የመተንፈሻ አካላት ሕመሞች እንዲሁም የስኳር በሽታ ተጠቃሽ ናቸው።ተላላፊ ባለሆኑ እነኚህ በሽታዎች በአለም አቀፍ ደረጃ በየአመቱ በሚሊዬን የሚቆጠሩ ሰዎች ህይወታቸውን እንደሚያጡ የአለም ጤና ድርጅት መረጃ ያመላክታል፡፡
በእነዚህ በሽታ ከሚሞቱት ሰዎች መካከል 85 በመቶ የሚሆኑት ዝቅተኛና መካከለኛ ገቢ ባላቸው አገራት መሆኑንም ጥናቶች ያሳያሉ፡፡ በኢትዮጵያ ከ52 በመቶ በላይ የሚሆኑ ዜጎች ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ሕይወታቸውን እንደሚያጡ የጤና ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል፡፡ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች በአሁኑ ወቅት በአገር አቀፍ ደረጃ ከሚከሰት ሞት ከግማሽ በላይ የሚሆነውን ድርሻ ይይዛሉ።
በየሰዓቱ ወደ 25 የሚገመቱ ኢትዮጵያውያን በስኳር፣ በኩላሊት፣ በጉበት፣ በልብና የደም ዝውውር በሽታዎች ምክንያት ህይወታቸውን ያጣሉ። ለዚህ አጋላጭ ከሚባሉ ምክንያቶች ውስጥ የአመጋገብ ስርዓት ዋነኛው መሆኑን የዘርፉ ባለሙያዎች እንዲሁም ጥናቶች ያመላክታሉ፡፡ በተለይም በፋብሪካ ተቀነባብረው ለምግብነት የሚውሉ ምርቶች ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች እንዲከሰቱ ምክንያት እንደሆነ ባለሙያዎይ ይናገራሉ።
ማህበረሰቡ የታሸጉ ምግቦች በውስጣቸው ስለያዙት ንጥረ ነገር እና መጠን አረጋግጦ የመግዛት ሁኔታ እንዳለ ሃሳባቸውን ለጣቢያችን የሰጡ ነዋሪዎች ተናግረዋል።አሁን ላይ ካለው የኑሮ ጫና እና ጊዜ በማጣት ምክንያት በብዛት የታሸጉ ምግቦችን እንደሚጠቀሙ እንዳሉ ይገለጻሉ፣ ይሁን እንጂ አብዛኛው ተጠቃሚዎች ምርቶቹ ለበሽታ አጋላጭ መሆናቸውን እንደማያውቁ ነው ያስታወቁት።
የጠቅላላ ሃኪም ዶ/ር አዜብ ሌሊሳ አሁን ላይ በፋብሪካ የተቀነባበሩ ምግቦችን ማህበረሰቡ በስፋት እየተጠቀመ እንዳለ ገልጸው፣ ይህም መሆኑ ዜጎች ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች ተጋላጭነት እንዲጨምር አድርጓል ብለዋል፡፡ በንፅፅር በከተሞች የሚኖሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ምርቶቹን በስፋት እንደሚጠቀሙ አስታውቀዋል።
ይህንኑ ሃሳብ የሚያጠናክሩት የስነምግብ ባለሙያዋ ቤተልሄም ላቀው አሁን ላይ የአኗኗር ዘይቤያችን እየዘመነ በመሆኑ ምግብን አብስሎ ከመጠቀም ይልቅ በፋብሪካ ተቀነባብረው ታሽገው የሚሸጡትን ማዘውተር እየተለመደ ነው ብለዋል።
እንደዚህ ዓይነት አመጋገብ ጥንቃቄ ካልታከለበት ለበሽታ የማጋለጥ እድሉ ሰፊ በመሆኑ፣ በተለይም ተጓዳኝ በሽታ ያለባቸው በቂ መረጃ ሊኖራቸው ይገባል ብለዋል፡፡ አብዛኛው ተጠቃሚ ስለ ሚገዟቸው ምግብች የሚገልጽ መረጃ ላለማየቱ ምክንያት የሚሆነው ምርቶቹ በተመረተባቸው ሀገራት ቋንቋ መፃፉ እና በውስጣቸው የሚገኙ ይዘቶችም ሳይንሳዊ አገላለጽ የሚጠቀሙ መሆኑን በማንሳት፣ ይህንን መረዳት የሚያስችል ፅሁፍ በሽፋናቸው ላይ እንዲኖር የሚመለከተው አካል ሊሰራበት ይገባል ሲሉ ሃሳባቸውን አሳፍረዋል፡፡
የተዋልዶ ጤና አገልግሎት ሰጪ ማህበራት ህብረት (ኮርሃ) ስራ አስፈፃሚ አቶ አበበ ከበደ በታሸጉና በተቀነባበሩ ምግቦች ምክንያት በእናቶችና ህጻናት ጤና ላይ የሚያስከትለውን ችግር ለማጥናት በዕቅድ መያዙን ተናግረዋል። አሁን ላይ የታሸጉና የተቀባበሩ ምግቦች በህጻናትና እናቶች ጤና ላይ ተፅዕኖ እያሳደረ መሆኑን ገልጸዋል።
ድርጅቱ የማህበረሰብ ጤናን የሚመለከቱ የተለያዩ ጉዳዮች ላይ ትኩረቱን አድርጎ እየሰራ እንደሚገኝ በመጥቀስ፣ ለሁሉም የጤና ጥቅሞች እንዲሁም የጤና እክሎች መነሻ የሆነው ስነ-ምግብ ወይንም አመጋገብ አንዱ እንደሆነ ተናግረዋል።
የጨው ፣ የስኳርና የስብ መጠናቸው ከፍተኛ የሆኑና ከመፈቀደው ደረጃ በላይ ከፍ ያለ ከሆነ በእርግዝና ወቅት በእናቶችና ህጻናት ላይ ከፍተኛ የጤና ጉዳት የሚያስከትል መሆኑ በጥናት መረጋገጡን አብራርተዋል። ህጻናት ወጣቶችና እናቶች ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች ያላቸው ተጋላጭነት መጨመሩን ተከትሎ፤ የህብረተሰቡን ግንዛቤ ለማሳደግና ችግሩን ለመፍታት እየተሰሩ መሆኑን አመላክተዋል።
ምንም እንኳን የታሸጉ ምግቦች በሙሉ የጤና ችግር የሚያስከትሉ ናቸው ባይባልም ደረጃቸውን ያልጠበቁና የተቀነባበሩ ብሎም ህጋዊነታቸው ያልተረጋገጡ ምግቦች እየተበራከቱ መሆኑን ገልጸው ፤ በተለይም ወጣቶች የታሸጉ ምግቦችን በስፋት እየተጠቀሙ በመሆኑ ጤናማ የሆነ የአመጋገብ ስርዓትን እንዲከተሉ የግንዛቤ ማስጨበጫ መረጃዎችን ለህብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ስራዎች መጀመራቸውን ስራ አስፈፃሚው አቶ አበበ ተናግረዋል።
ዜጎች ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ማረጋገጫ ያላገኙና ደረጃቸውን ያልጠበቁ የታሸጉ ምግቦችን እንዳይጠቀሙ ለማድረግ የሚያስችሉ ትምህርታዊ መድረኮችን ለማዘጋጀት ስትራቴጂ መዘጋጀቱንም ገልጸዋል፡፡
በተጨማሪም የተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን አማራጮችን በመጠቀም የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን ለመስራት በዕቅድ መያዙንና አሁን ላይ እየተዘጋጀ ያለው የታሸጉ ምግቦችን መቆጣጠር የሚያስችል ረቂቅ አዋጅ እንዲጸድቅና ወደስራ እንዲገባ እየተሰራ መሆኑን ተናግረው ፤ አዋጁ ከጸደቀም በኋላ በሚዘጋጁ መመሪያዎች በመታገዝ ወደሰራ እንዲገባ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በጋራ ለመስራት ጥረቶች እንደሚደረጉ አመላክተዋል፡፡
በአብዛኛው ለኩላሊት ህመም የተጋለጡ ሰዎች ለስኳር እና የደም ግፊት በመጋለጣቸው እንደሆነ የሚገልጹት ደግሞ የኢትዮጵያ የኩላሊት ንቅለ ተከላ ማህበር ሰብሳቢ አቶ ቢኒያም አበራ ናቸው፡፡
ለደም ግፊት እና ለስኳር አጋላጭ የሚሆኑት የታሸጉ ምግቦች በውስጣቸው በሚይዙት የስኳር እና የጨው መጠን በመሆኑ ጤናማ ያልሆነ አመጋገብ ቁጥጥር ረቂቅ አዋጅ በአፋጣኝ እንዲፀድቅ ማህበሩ ጥሪ ማቅረቡን አብራርተዋል።
ሌላኛው በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የውስጥ ደዌና የስኳር ሆርሞኖች ህክምና እስፔሻሊስት እና የስኳር ህሙማን ማህበር አማካሪ ዶ/ር ቴድሮስ አበራ፣ የስኳር በሽታ በቤተሰብ የሚተላለፍበት ሁኔታ መኖሩን እና በሌላ በኩል ደግሞ ከአመጋገብ ስርዓት ጋር ተያይዞ በተለይም በፋብሪካ ተቀነባብረው ታሸገው የሚሸጡ ምግቦች አጋላጭ መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡
በተለይም በውስጣቸው የሚይዟቸው ንጥረ ነገሮች ላልተፈለገ ውፍረትም የሚያጋልጡ መሆናቸውን እና አሁን ላይ የስኳር በሽታም እየተስፋፋ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የአመጋገብ ስርዓታችን ከስኳር በሽታ ባለፈም ለሌሎች ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች በስፋት እያጋለጠ በመሆኑ ትኩረት ተሰጥቶ ሊሰራበት እንደሚገባ ገልፀዋል፡፡
በጤና ሚኒስቴር የበሽታዎች መከላከልና መቆጣጠር ስራ አስፈጻሚ ዶ/ር ሙሴ ገ/ሚካኤል በበኩላቸው ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች እንደሃገር ካላቸው ከፍተኛ ጫና አንጻር በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸው፤ የህክምና ባለሙያዎች የስልጠና መመሪያ መዘጋጀቱንና ከ1ሺ በላይ ለሚሆኑ የጤና ተቋማት የባለሙያ ስልጠና ሲሰጥ መቆየቱን፣ በዚህም የህክምና ባለሙያዎች ወደ መሰረታዊ የጤና ተቋማት ወርደው ለሁሉም ማህበረሰብ ተደራሽ እንዲያደርጉ መሰራቱን አብራርተዋል።
ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች አጋላጭ ከሆኑት ምክንያቶች አንዱ የታሸጉና ጤናማ ያልሆኑ ምግቦች በመሆናቸው ቁጥጥር ለማድረግ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር የተዘጋጀው ረቂቅ ላይ ውይይቶች እየተደረጉ መሆኑን እና አዋጁ ከፀደቀ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ስርጭትን ለመቀነስ እንደሚረዳ ገልፀዋል፡፡
ረቂቅ አዋጁ ሙሉ ለሙሉ የታሸጉ ምግቦች እንዳይሸጡ የሚከለክል ሳይሆን መሸጥ የሚችሉባቸውን ቦታዎችን የሚለይ ነው ተብሏል። ለአብነት ትምህርት ቤቶች አካባቢ ወይም ትምህርት ቤቶች ውስጥ እንዳይሸጡ እንዲሁም ይዘታቸው ግልፅ በሆነ ሁኔታ እንዲፃፍ የሚያስገድድ መሆኑ ተመላክቷል፡፡
ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ስርጭት ለመቀነስ ማህበረሰቡ ያለው ግንዛቤ እንዲሻሻል እና ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡም ሆነ በሀገር ውስጥ የሚመረቱ ምግብ ነክ ምርቶችም፣ ይህንን በግልፅ የማሳወቅ ግዴታቸውን እንዲወጡ ለማስቻል በረቂቅ ደረጃ የሚገኘው አዋጅ ሊፀድቅ እና በአፋጣኝ ተግባራዊ ሊደረግ እንደሚገባው በዳሰሳው የተሳፈሩ አካላት አፅንዖት ሰጥተውበታል፡፡

ምላሽ ይስጡ