ሰኔ 17 ቀን 2017(መናኸሪያ ሬዲዮ) የኢራን የፀጥታ ምክር ቤት ከእስራኤል ጋር የተኩስ አቁም ስምምነት መደረሱን ማረጋገጡን የሀገሪቱ የመገናኛ ብዙኃን ዘገቡ። ይህ ውሳኔ የመጣው ለ12 ቀናት የዘለቀው እና የመካከለኛው ምስራቅን ክልል ወደ ከፍተኛ ግጭት ሊያስገባ የነበረውን ውጥረት ተከትሎ ነው።
የኢራን የፀጥታ ምክር ቤት ባወጣው መግለጫ፣ ከአሁን በኋላ ወታደራዊ እርምጃ እንደማይወስድ ገልጿል። ይሁን እንጂ፣ የእስራኤል ወገን ህገ-ወጥ ጥቃቶቹን ካላቆመ፣ ኢራን ምላሽ ለመስጠት እንደምትገደድ አስጠንቅቋል።
የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ቀደም ሲል በእስራኤል እና በኢራን መካከል የተኩስ አቁም ስምምነት መደረሱን ይፋ አድርገው ነበር። ትራምፕ ስምምነቱን “ሙሉ እና አጠቃላይ የተኩስ አቁም” ሲሉ ገልጸውት፣ ሁለቱም ወገኖች ስምምነቱን እንዳይጥሱ አሳስበዋል።
የተኩስ አቁሙ ስምምነት የተፈጠረው በኳታር መንግስት አማላጅነት መሆኑ ታውቋል። የኳታር ጠቅላይ ሚኒስትር ሼክ መሀመድ ቢን አብዱልራህማን አል ታኒ ከኢራን ባለስልጣናት ጋር በመነጋገር ስምምነቱን ለማረጋገጥ ወሳኝ ሚና ተጫውተዋል።
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ባለፈው ሰኞ እንዳሉት ከእስራኤል ጋር ምንም አይነት “ስምምነት” ባይኖርም፣ እስራኤል ህገ-ወጥ ጥቃቶቿን ካቆመች ኢራን ምላሽ መስጠቷን እንደምታቆም ተናግረው ነበር። ሆኖም፣ ከትራምፕ ማስታወቂያ በኋላም ቢሆን፣ ሁለቱ ሃገራት ጥቃት መሰናዘራቸውን እንዳላቆሙ መረጃዎች ያመለክታሉ።
ይህ የተኩስ አቁም ስምምነት የመካከለኛው ምስራቅ ውጥረትን ለማርገብ ወሳኝ እርምጃ ቢሆንም፣ የሁለቱ ወገኖች ሙሉ በሙሉ ስምምነቱን አክብረው እንደሚቀጥሉ የሚጠበቅ ይሆናል። ዓለም አቀፉ ማህበረሰብም ሁኔታውን በቅርበት እየተከታተለ ሲሆን፣ በክልሉ ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ ጥሪውን አቅርቧል።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
👉011-639-28-52
👉011-639-37-63
ምላሽ ይስጡ