ህጻናት ለሚገባቸው ፍትህ ተገቢውን ትኩረት ሰጥቶ በመስራት ረገድ የሚመለከታቸው አካላት በቅጡ እየሰሩ እንዳልሆነ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ለመናኸሪያ ሬዲዮ አስታውቋል።
ዛሬም ድረስ በኢትዮጵያ በርካታ ፍትህ የሚሹ፣ መሠረታዊ መብቶቻቸው ያልተከበረላቸው ህጻናት መኖራቸውን በኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን የሴቶች፣ ህጻናት፣ አካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን መብቶች ኮሚሽነር ወ/ሮ እርግበ ገብረሃዋርያት ለመናኸሪያ ሬዲዮ ተናግረዋል።
ህጻናትን በሚመለከቱ ጉዳዮች ትክክለኛ የህጻናት ተሳትፎና ተገቢው ውክልና በስፋት አይስተዋልም ያሉት ኮሚሽነሯ፣ መብቶቻቸው በሌሎች የሚወሰኑና የሚደነገጉ በመሆኑ ተሳትፏቸውና ተደማጭነታቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ ከመሻሻል ይልቅ አጣብቂኝ ውስጥ መሆኑን ገልጸዋል።
ጥቂት የማይባሉ ህጻናት ለጉልበት ብዝበዛ ሲዳረጉ፣ ለአካላዊ ጥቃት ሲጋለጡ እንደቆዩና ተመሳሳይ አካሄዶች እንደ ሀገር እንደቀጠሉ አስታውቀዋል።
በተለይም ከ15 አመት በታች በሆኑ ህጻናት ላይ የሚደርሰው ጥቃትና የጉልበት ብዝበዛ የተቋማትን ትኩረት የሚሻ መሆኑን ነው ኮሚሽነር እርግበ የተናገሩት።
ኢትዮጵያ እንደ ሀገር የተቀበለቻቸው አለም አቀፍ የህጻናት መብቶችና ድንጋጌዎች ቢኖሩም አስፈጻሚ አካላት በቂ ትኩረት ባለመስጠታቸው ደካማ አፈጻጸም እንደሚስተዋል ተናግረዋል።
ኮሚሽኑ በተደጋጋሚ ጊዜ የደረሰባቸውን ጥናቶችና ሪፖርቶች ለሚመለከታቸው አካላት ቢያሳውቅም ምክረሃሳቦችን በመተግበር በኩል አናሳ አፈጻጸም መኖሩንም ነው ኮሚሽነሯ የገለጹት።
የአፍሪካ የህጻናት ቀን ዘንድሮ በአፍሪከ ለ35ኛ ጊዜ በሀገራችን ደግሞ ለ34ኛ ጊዜ በዛሬው እለት በተለያዩ ስፍራዎች ተከብሮ እንደሚያልፍ ይታወቃል። በአጠቃላይ የህጻናት ቀን፡ የአለም የህጻናት ቀን እና የአፍሪካ የህጻናት ቀን በሚል በዓመት ሁለት ጊዜ እንደሚከበርም ይታወቃል።
ምላሽ ይስጡ