ሰኔ 02 ቀን 2017(መናኸሪያ ሬዲዮ) የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ ላይ መራጮችና ዕጩዎች ካሉበት ሆነው በኦንላይን መመዝገብ የሚችሉበት ሶፍትዌር ማበልፀጉን አስታወቀ፡፡
ቦርዱ 7ኛውን ሀገራዊ ምርጫ በቴክኖሎጂ ታግዞ የመራጮችም ሆነ የዕጩ ተወዳዳሪዎችን ምዝገባ ማከናወን በሚያስችለው የቴክኖሎጂ አሥተዳደር ሥርዓት ላይ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር እየመከረ ነው፡፡
የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላተወርቅ ኃይሉ በዚሁ ወቅት፤ ተቋማቸው የምርጫ ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ማድረግ የሚያስችለውን ሥራ ሲያከናውን መቆየቱን አስረድተዋል፡፡
የዛሬው ውይይትም ይህን በቴክኖሎጂ የታገዘ የምርጫ አሥተዳደር ሥርዓት ለፖለቲካ ፓርቲዎች አቅርቦ ሐሳብና ግብዓት ለመሰብሰብ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ያለፉት ሥድስት የኢትዮጵያ የምርጫ ሂደቶች ማንዋል እንደነበሩ አውስተው፤ በ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ መራጮችም ሆኑ ዕጩዎች ካሉበት ሆነው በኦንላይን መመዝገብ የሚችሉበትን ሶፍትዌር ማበልፀግ መቻሉን አስታውቀዋል፡፡
ሂደቱ ኢትዮጵያ በምርጫ ሥርአቷ አንድ እርምጃ ወደፊት መራመድ የሚያስችላት ከመሆኑ ባለፈ፤ በምርጫው ሂደት ላይ ግልፅነትና ተጠያቂነትን ለማስፈን ያስችላል ነው ያሉት።
የውይይቱ ተሳታፊ የፖለቲካ ፓርቲዎች በበኩላቸው ሶፍትዌሩ ጊዜ ቆጣቢና እንግልት የሚቀንስ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለግልፅነትና ለተጠያቂነት ምቹ መደላድል እንደሚፈጥር ተናግረዋል፡፡
ፋሚኮ
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ