በውጭ ሀገር የስራ ስምሪት ብቁ ያልሆኑ ዜጎች እየተላኩ በመሆኑ ለስቃይ መዳረጋቸውን የፌደራል የስነ-ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽን ጥናት ገለጸ።
ይህንን በተመለከተ የወጣው አዋጅ ለውጭ አገር የስራ ስምሪት የሚሔዱ ዜጎች በትንሹ የአንድ ወር በቂ ስልጠና እንዲያገኙ ቢደነገግም፤ በሁለት እና ሶስት ቀናት ስልጠና የሚላኩ በርካታ ዜጎች መኖራቸውን በፌደራል ስነ-ምግባርና ጸረ-ሙስና ኮሚሽን የአስቸኳይ ሙስና መከላከል ዴስክ ሃላፊ ወ/ሮ ቀጸላ መንግስቱ ለመናኸሪያ ሬዲዮ ተናግረዋል።
ብቁ ያልሆኑ ዜጎች ወደ ውጭ ሀገር እየተላኩ እንደሚገኙ በጥናት መረጋገጡን የተናገሩት የዴስክ ሃላፊዋ፤ ለዚህም ዋነኛ ተዋናዮች ኤጀንሲዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። ስልጠናውን ሳያገኙ በአቋራጭ ወደ ውጭ ሀገር ሰራተኞችን የሚልኩ ኤጀንሲዎችን ስራና ክህሎት ሚኒስቴር በአግባቡ እየተቆጣጠረ አይደለም ሲሉም ገልጸዋል።
ኤጀንሲዎች ከሀገር ውስጥ እስከ ውጭ በተዘረጋ ሰንሰለት የተሻለ ስራ ታገኛላችሁ በሚል የስራ ቦታቸውን በየጊዜው በመቀያየር በህገወጥ መልኩ ወደ ውጪ እንደሚልኳቸው ተናግረዋል፡፡
በዚህ አሰራራቸው ዜጎች ከመንግስት እውቅና ውጭ ጉዳት ሲደርስባቸው የሚደርስላቸው እንዳይኖር እያደረጉ እንደሚገኙ በጥናት ተረጋግጧል ሲሉ ወ/ሮ ቀጸላ ተናግረዋል። የነቁና የበቁ ዜጎች ለውጭ ሀገር የስራ ስምሪት እየተላኩ ባለመሆኑ ኢትዮጵያውያን ከሌሎች ሀገራት ዜጎች አንጻር ዝቅተኛ ክፍያ እንዲከፈላቸው ሆኗል ብለዋል።
ህጋዊ የመንግስት ስልጣን ያለው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ህገ ወጥ ሰንሰለቱን መቆጣጠርና መቀነስ እንደሚገባው በጥናቱ መመላከቱን የተናገሩት ኃላፊዋ፤ ህገ ወጥ የሆነው የኤጀንሲዎች አሰራር የሚቀጥል ከሆነ ዜጎች በመንግስት ህጋዊ የስራ ስምሪት ሂደት ላይ አመኔታ እንዲያጡ ያደርጋል ሲሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡
ከዚህ ቀደም የስራና ክህሎት ሚኒስቴር የአረብ ሀገራት ለኢትዮጵያውያን የሚከፍሉትን ዝቅተኛ የደመወዝ መጠን ለማሻሻል ከቀጣሪ ሀገራቱ ጋር እነጋገርበታለሁ ማለቱ የሚታወስ ነው።
__
ሀሳብ እና’ሳ’ፍራለን
ምላሽ ይስጡ