በማይናማር የሚገኙ ዜጎችን ማስመለሱ ቢቀጥልም አሁንም በህገ ወጥ መንገድ ወደ ስፍራው የሚያቀኑ ዜጎች መበራከታቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።
በዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ ስራ ኢትዮጵያ በተለያዩ ሀገራት በእንግልት ላይ የሚገኙ ዜጎቿን እያስመለሰች እንደምትገኝ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነቢያት ጌታቸው ተናግረዋል። በተለይ በማይናማር የሚገኙ ዜጎችን የማስመለሱ ስራ ቅድሚያ ትኩረት እንደተሰጠው በመግለጽ እስካሁን 7መቶ ያህል ዜጎች መመለሳቸውን አምባሳደር ነቢያት ገልጸዋል። ይሁን እንጂ አሁንም በተለያዩ ህገ ወጥ ደላሎች አማካኝነት በጥቅሉ የውጭ ሀገር የስራ ስምሪት እንከን እየገጠመው እንደሚገኝ አምባሳደር ነቢያት ተናግረዋል።
ዜጎች አሁንም በህገ ወጦች እየተታለሉ ወደማይናማር እየተጓዙ መሆኑ ችግሩን እንዳባባሰው ቃል አቀባዩ ገልጸዋል። በማይናማር ያሉ ዜጎችን ለማስመለስ መንግስት በህንድ ኒው ደልሂ ባለው የኢትዮጵያ ኢንባሲ አማካኝነት እየሰራ እንደሚገኝም ነው የተገለጸው።
ዜጎችን ለህገ ወጥ ስደት የሚዳርጉ ደላሎችን ለመከላከል በጋራ ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት በተጨማሪ መገናኛ ብዙሃኑም ተገቢውን መረጃ በማጋራት አዎንታዊ ሚናቸውን ማስቀጠል አለባቸው ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባዩ አመላክተዋል።
ምላሽ ይስጡ