ኢትዮጵያ የተቀቀለ ስጋ ለቻይና ልትልክ መሆኑን የኢትዮጵያ ግብርና ባለስልጣን አስታወቀ።
የኢፌደሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደር እና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኢትዮጵያ የግብርና ባለስልጣን የእንስሳት ቄራዎች አደረጃጀት እና የስጋ ምርት አገልግሎት አሰጣጥ ውጤታማነት በተመለከተ የተከናወነ ክዋኔ ኦዲት ሪፖርትን መነሻ በማድረግ ውይይት አካሂዷል።
በውይይቱ ወቅት የግብርና ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አምባሳደር ድሪባ ኩማ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ ሞጎሊያን ጨምሮ ከተለያዩ ሀገራት ተሞክሮ በመውሰድ የተቀቀለ ስጋ ለቻይና ለማቅረብ እየሰራች ነው።
ኢትዮጵያ የቻይናን ትልቅ የስጋ ምርት ገበያ ለመጠቀም ዝግጅቷን ማጠናቀቋን አመላክተዋል።
ኢትዮጵያ የስጋ ምርትን ቻይና መላክ ከጀመረች ከቻይና የገበያ መስፈረት ጋር ተመሳሳይ ለሆኑት የአውሮፓና ኤዥያ ገበያ ማቅረብ እንደምትችልም ገልጸዋል።
በቻይና ሀገር የምርት ጥራትና ደህንነት በሚቆጣጠረው ተቋም የሚሰሩ ባለሙያዎች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው የኢትዮጵያን የስጋ አመራረት መመልከታቸውን አስታውቀዋል።
የቻይናው ተቋም ለኢትዮጵያ የላከው ከአንድ ሺህ በላይ ገጽ ያለው ዶክመንት በኢትዮጵያ ባለሙያዎች ተሞልቶ መላኩን ገልጸው፤ በቅርቡ ምላሽ ይልካሉ ተብሎ ይጠበቃል ነው ያሉት።
ኢትዮጵያ የተቀቀለ ስጋን ወደ ቻይና ስትልክ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር ማግኘት እንደምትችል ተናግረዋል።
ቻይናዎች የሚፈልጉት ከበሽታ ነጻ የሆነ የእንስሳት አረባብ መሆኑን ገልጸው፤ በኢትዮጵያ ከበሽታ ነጻ የሆኑ እንስሳትን ለማርባት እየተሰራ ነው ብለዋል።
በሌላ በኩል የቻይናን ገበያ በስፋት ለመጠቀም ብዙ ቄራዎችን መገንባት እንደሚገባ ተናግረዋል።
ኢፕድ
ምላሽ ይስጡ