የኢትዮጵያ ሰራተኞች ማህበራት ኮንፌዴሬሽን በበኩሉ በክልሉ ከከሰም የስኳር ፋብሪካ የተፈናቀሉ ሰራተኞችን በተለያዩ ፋብሪካዎች ለማሰማራት የታቀደ ቢሆንም፤ ፋብሪካዎቹ ካላቸው የሰራተኛ ቁጥር አንጻር ማሳካት እንዳልተቻለ አስታውቋል፡፡
መናኸሪያ ሬዲዮ ያነጋገራቸው በክልሉ የገቢ ረሱ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዶ አሊ በአሁኑ ሰዓት የመሬት መንቀጥቀጥ አደጋው የመቀነስ አዝማሚያዎች እንዳሳየ ገልጸዋል፡፡
በዚህም ባለፉት ጊዜያት የመሬት መንቀጥቀጥ አደጋው በስፋት በተስተዋለባቸው አካባቢዎች ጥናቶች እየተከናወኑ መሆኑን እና ከጥናቱ መጠናቀቅ በኋላ ውጤቱን በማየት የተፈናቀሉ ዜጎች ለመመለስ ጥረት ይደረጋልም ብለዋል፡፡
አሁንም ድረስ የተፈናቀሉ ዜጎች በተዘጋጀላቸው መጠለያ ጣቢያ ቢኖሩም የመሬት መንቀጥቀጥ አደጋው የመቀነስ አዝማሚያዎች በማሳየቱ የመመለስ ፍላጎት እንዳላቸው ነው የተናገሩት፡፡
አያይዘውም ባለፉት ጊዜያት በክልሉ የተከሰተውን የመሬት መንቀጥቀጥ አደጋ ተከትሎ የከሰም ስኳር ፋብሪካ ጉዳት እንደደረሰበት አስታውሰው፤ በባለሙያዎች በኩል እየተደረገ ያለውን ጥናት ተከትሎ ፋብሪካውን ወደ መደበኛ ስራው እንደሚመለስ ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሰራተኛ ማህበራት ኮንፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ በተፈጥሮ አደጋ ምክንያት ከከሰም የስኳር ፋብሪካ የተፈናቀሉ ዜጎችን ወደ ሌሎች ፋብሪካዎች ለማዘዋወር ጥረት ቢደረግም በቂ የሰው ሃይል ያላቸው በመሆኑ እና ክፍት ቦታ ማግኘት ባለመቻሉ ስራውን ማከናወን አልተቻለም ብለዋል፡፡
ይሁን እንጂ አሁንም ድረስ ኮንፌዴሬሽኑ ለሚመለከታቸው አካላት ደብዳቤ በመጻፍ አማራጭ መፍትሄዎች እንዲመቻቹ እየጠየቀ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
በኢትዮጵያ በተለያዩ ቦታዎች የተፈጥሮ አደጋዎች እያጋጠሙ ሲሆን በአፋር ክልል የተከሰተው የመሬት መንቀጥቀጥ አደጋ አንዱ ተጠቃሽ ነው፡፡
__
ምላሽ ይስጡ