የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በትግራይ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ ዙሪያ በኢትዮጵያ ከሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ አባላት ጋር ውይይት እያካሄደ ነው።
ውይይቱ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) እና የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ርዕሰ መስተዳድር ጌታቸው ረዳ እየተመራ ይገኛል።
በመድረኩ ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር)፤ ራሱን ነጥሎ የወጣው የህወሓት አንጃ የፕሪቶሪያው ስምምነት ሙሉ ለሙሉ እንዳይተገበር እንቅፋት መሆኑን ገልጸዋል።
በተጨማሪም ምርጫ ቦርድ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያካሄድ የሰጠውን መመሪያ አለመቀበሉን አስረድተዋል።
የፌደራል መንግስት የፕሪቶሪያው ስምምነት ሙሉ ለሙሉ እንዲተገበር እየሰራ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ መንግስት የክልሉን ወቅታዊ ሁኔታ በጥሞና እየተከታተለ ነው ብለዋል፡፡
ዓለም አቀፉ ማህበረሰብም በክልሉ የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት አስፈላጊውን እገዛ እንዲያደርግ ጥሪ አድርገዋል፡፡
በክልሉ ወቅታዊ የሰላም እና ፀጥታ ዙሪያ ማብራሪያ የሰጡት አቶ ጌታቸው ረዳ በበኩላቸው፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ራሱን ነጥሎ የወጣው የህወሓት አንጃ የጊዜያዊ አስተዳደሩ የዕለት ተለት ተግባራት ላይ እክል እየፈጠረ መምጣቱን አስረድተዋል።
ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እና የፌደራል መንግሥት በክልሉ ዘላቂ ሰላም ግንባታ ያላቸውን ሚና አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጥሪ ማቅረባቸውን ፋ.ሚ.ኮ ዘግቧል።
ምላሽ ይስጡ